January
31, 2015
ግሩም
ድንቅ ሆኜ ተፈጥሬአለሁ
ብዙ ሰዎች “ሳይንስና እምነት አብረው አይሄዱም፣አይስማሙም
” ተብሎ ሲነገር እሰማለሁ፡፡እኔ ግን ሳይንስና እምነት ይደጋገፋሉ ብዬ አስባለሁ፣አምናለሁም፡፡ሳይንስ የእግዚአብሔርን ሥራ በሚገባ
ጎልቶ እንዲታይ ያደርጋል የሚልም አመለካከት አለኝ፡፡ዕውቁ ሳይንቲስት አልበርት አንስታይን “Science without religion is lame,religion without science is blind”/ “ሳይንስ
ያለ እምነት አንካሳ ነው፤እምነት ያለ ሳይንስ እውር ነው” ብሏል፤ሳይንስና እምነት አብረው እንደሚሄዱና እንደሚደጋገፉ ለማሳየት!
የሕክምና ባለሙያ ስለሆንሁ ስለ ሰው አፈጣጠር፣የአካል
ቅንብርና አሠራሮችን ለማጥናት ዕድለኛ ሆኛለሁ፡፡በነዚህ አጋጣሚዎች የሰው ልጅ እጅግ ከፍ ባለ ጥበብ እንደተፈጠረ ለመገንዘብ ችያለሁ፡፡ከአእምሮ
በላይ የሆነ እውቀት እንደሠራውና እንዳበጀው ምንም ጥርጥርም የለኝ፡፡ዘወትርም የሰውን አካላዊ ቅንጅትና አሠራር ሳስብ፣እግዚአብሔርን
በነገሮቹ ውስጥ ስለማይ በምስጋናና በግርምት እሞላለሁ፡፡እጅግ የሚገርመው እያንዳንዱ በየቦታው የተሰካካው የአካል ክፍል በዓላማ
የተሰካና ከሌላው ጋራ በሕብር ተስማምቶ የሚሠራው ሥራ መኖሩ ነው፡፡እነዚህን የላቁ አካላዊ ቅንብሮችና ቅንጅቶች ማሰላሰሌም ለአምነቴ
መጠንከርና መነቃቃት ግሩም ምክንያት ሆኖኛል፡፡ብዙ ጊዜም ምስጋና ፈንቅሎኝ፣“ተመስገን የጥበብ ሁሉ አምላክ ተባረክ” እላለሁ፡፡እስቲ
ሥራዎቹን በተናጠል ለአብነት ልዳስስ፡፡
የልብ ያለ ማቋረጥ መምታቱ፣ደም ከአንዱ የልብ
ክፍል ወደ ሌላው ሂደቱን በጠበቀ መልኩ መፍሰሱ፣እያንዳንዱ የልብ ክፍል ክዳኖች በራሳቸው ጊዜ መከፈት መዘጋታቸው፣እናም ልብ ያለ
ማቋረጥ እየሠራ አለ መድከሙ እጅግ ይገርመኛል፡፡
አንድ ሳይንቲስ “ኩላሊት እጅግ በጣም የረቀቀ
የኬሚካል እንደስትሪ ነው” ብለው ተናግረዋል፡፡እስማማለሁ፡፡በሰውነታችን ውስጥ ባለው ሂደት ደም ውስጥ ያለው አብዛኛው ንጥረ ነገር
ቆሻሻን ጨምሮ፣መጨረሻ ላይ የሚያልፈው በኩላሊት በኩል ነው፡፡ኩላሊት ደግሞ ለሰውነት የሚጠቅምና የማይጠቅመውን ለይቶ፣ የማይጠቅመውን ብቻ
ያስወግዳል፡፡ሰውነታችንን የሚጠቅሙ ንጥረ ነገሮችና ኬሚካሎች፣ወደ ደም ተመልሰው ሰውነታቸንን ያገለግላሉ፡፡ይገርማል፡፡
ሌላ እጅግ የሚገርመኝ ነገር፣የማሰባችን ጥበብ ነው፡፡አንድ ሰው ስለ
አንድ ጉዳይ ጠይቆን ለጊዜው ማስታወስ ባንችልም፣ከተጠየቅንበት ሰዓት ጀምሮ አእምሮአችን ያንን ጉዳይ ሊያስታውሰን በመፈለግ ይባትላል፡፡ከዚያም
ያ ለማስታወስ የተቸገርነው ነገር ከሰዓታት ወይም ከቀናት በኋላ ትዝ ይለናል፡፡አእምሮ ከድብቅ ማሕደሩ (subconscious) ሲፈልግ
ከርሟላ!
ሴት ልጅ ዘጠኝ ወር ማርገዟን እናውቃለን፡፡የሚደንቀው ነገር የሚከተለው
ነው፡፡ሳይንቲስቶች ሴትየዋ ልክ የመውለጃዋ ጊዜ ሲደርስ፣ምጧ የሚጀመርምበትን መንስኤና ምክንያት እስከ አሁን ሊያውቁ አልቻሉም፡፡ሰዓቱን
ጠብቆ ከች ማለቱ እጅግ ገራሚ ነውና፡፡ማህፀን ጊዜና ሰዓት የተገጠመለት ይመስል፣ምንም ሳያሳትት በትክክለኛው ጊዜ ልጁን ለማስወጣት
መንቀሳቀስ ይጀምራል፡፡የምጥ አጀማመር ቅንብሩ፣እየጨመረ የሚሄደው የማህፀን አከፋፈት፣ማህፀን ከላይ ልጁን እየገፋ ጸንሱ እስኪወጣ
ድረስ አለ ማቋረጡ ይገርማል፡፡ማህፀን ጽንሱን ካስወጣ በኋላ ወደ ቀድሞ ቦታው፣ቅርጹና መጠኑ መመለሱ ሌላው ገራሚ ነገር ነው፡፡ጸንሱ
በማህፀን ሳለ የአመጋገብ ስርዓቱ፣በተመቸ ከባቢ ሳይጨናነቅ ተመችቶት በውኃ ላይ እየተንሳፈፈ ማደጉ እጅግ አስደናቂ ጥበብ ነው፡፡
በሰውነታችን ላይ የምግብ የማንሸራሸር ስርዓት ይገርመኛል፡፡ሰው በአፉ
ጐርሶ ማኘክ የጀመረው ምግብ መድቀቅ የሚጀመረው እዛው አፉ ውስጥ ነው፡፡በተለያዩ ተፈጥሮአዊ ኬሚካሎች(ኢንዛይሞች) መሰባበርና መላም
ቢጀምርም፣ብዙ ርቀት እየላመ ይጓዛል፡፡ጨጓራ ውስጥ አሲድ ባለው ከባቢ በማለፍ የበለጠ እየላመና እየተጨመቀ ይሄዳል፡፡በትንሹ አንጀትም
ውስጥ እንዲሁ፡፡ብዙ ኬሚካላዊ ሂደቶች ውስጥ አልፎ፣እጅግ የላሙ፣ለሰውነታችን የሚጠቅሙ ነገሮች ሁሉ፣አንድም ሳይቀሩ ወደ ደማችንን
ይገባሉ፡፡የማይጠቅመው ነገር በትልቁ አንጀታችን በኩል አልፎ ወደ ውጭ ይወጣል፡፡ይገርማል፡፡
ሳይንቲቶች የአእምሮአችንን ውስብስብ ተፈጠሮአዊ አሠራር፣ገና በሚገባ
እንዳልተገነዘቡት በተለያዩ ጽሑፋቸው ላይ ይናገራሉ፡፡ባንዴ በጣም ውስብስብ ሥራን ከሚሠሩ ብዙ ኮምፒዩተሮች የበለጠ ልቀት አለው፡፡ከልጅነት
እስከ ሽምግልና ያሉ ያወቅናቸውንና ያየናቸውን ክስቶቶች፣ታሪኮችን፣ቃሎች ወዘተ ማስታወስ ይችላል፡፡ባንዴ በርከት ያሉ ሥራዎችን የመሥራት
ብቃት አለው፡፡እጆቻችን፣እግሮቻችን፣አይኖቻችንንና ጭንቅላታችን በሕብር እንዲንቀሳቀሱ ይመራል፣ያቀናጃልም፡፡እስቲ አስቡት አንድ መኪና
የሚነዳ ሰው፣በውጭ ያሉ የሌሎች መኪናዎችን እንቅስቃሴ እያየ ይቆጣጠራል፡፡በእግሩ ደግሞ የነዳጅ መስጫና ፍሬኑን በእግሩ ይቆጣጠራል፡፡እግረ
መንገዱን ሙዚቃ ወይም ዜና ከፍቶ እያዳመጠ ይሄዳል፡፡እጆቹ መሪ ይዘው የመኪናውን አቅጣጫ ይቆጣጠራሉ፡፡ይህንን ሁሉ በሕብር የሚያቀናጀው
አእምሮ ነው፡፡ባንዴ ከስድስት በላይ ሥራዎች፡፡ይገርማል፡፡
ይህ ሁሉ የጠቀስሁት የጥበብ ሥራ ከላይ ፈጣሪና አቀናባሪ እንዳለ ይናገራል፡፡እንዲሁም
ከፍ ያለ እጅና ጥበብ እንዳለ በሚገባ ይመሰክራል፡፡ለዚህ ነው ዳዊት ይህንን በመንፈስ አስተውሎ እንዲህ ያለው፡-
“አቤቱ፣አንተ ኵላሊቴን ፈጥረሃልና፣በእናቴም ሆድ ሰውረኸኛል። ግሩምና ድንቅ ሆኜ ተፈጥሬአለሁና አመሰግንሃለሁ፤ ሥራህ ድንቅ ነው፣ነፍሴም እጅግ ታውቀዋለች። እኔ በስውር በተሠራሁ ጊዜ፣አካሌም በምድር ታች በተሠራ ጊዜ አጥንቶቼ ከአንተ አልተሰወሩም። ያልተሠራ አካሌን ዓይኖችህ አዩኝ፤የተፈጠሩ ቀኖቼ ሁሉ አንድ ስንኳ ሳይኖር በመጽሐፍህ ተጻፉ” (መዝመር 139፡13-16)
ዳዊት
“ግሩምና ድንቅ ሆኜ ተፈጥሬአለሁ” ሲል ከላይ
የጠቃቀስኳቸውን የሰው ልጅ ውስብስብ ተፈጥሮአዊ አሠራሮችን በመንፈሱ ተረድቶ እንደ ሆነ እገምታለሁ፡፡“ነፍሴም ታውቀዋለች” ብሎ የተናገረው አገላለጽ ያስደንቀኛል፤ውስጣዊ መረዳት እንደሚያስፈልገን ሲጠቁመን! እርግጥ ነው፣ይህን
ለመረዳት የነፍስ እውቀት ይፈልጋል፡፡የዓይን ብርሃን ይፈልጋል፡፡
ሐዋርያው
ጳውሎስም የእግዚአብሔር ጥበብ እጅግ አስደንቆት፣መልዕክቱን አቋርጦ፣እንዲህ ብሎ ውዳሴን አቅርቧል፡-
“የእግዚአብሔር ባለ ጠግነትና ጥበብ እውቀቱም እንዴት ጥልቅ ነው፤ ፍርዱ እንዴት የማይመረመር ነው፥ ለመንገዱም ፍለጋ የለውም። የጌታን ልብ ያወቀው ማን ነው? ወይስ አማካሪው ማን ነበር? ወይስ ብድራቱን ይመልስ ዘንድ ለእርሱ አስቀድሞ የሰጠው ማን ነው? ሁሉ ከእርሱና በእርሱ ለእርሱም ነውና፤ ለእርሱ ለዘላለም ክብር ይሁን፤ አሜን።” (ሮሜ 11፡33-36)
እግዚአብሔር
ረድቶትና ዓይኑ ተከፍቶ ላስተዋለ፣የእግዚአብሔር የጥበብ ሥራ እጅግ አስገራሚ ነው፡፡አንድ ሽማግሌ እንዳሉት
“ልበ ብርሃን” መሆን ነው የሚያስፈልገው፡፡አዎ! የልቡናው ዓይን የበራለት ሰው፣እነዚህን የጥበብ ሥራዎች ዐይቶ፣ተገቢው የሆነውን
ክብር ለአምላኩ ይሠጣል፡፡የምስጋና ሰው ይሆናል፡፡ሕይወቱ በአድናቆትና በመገረም ይሞላል፡፡ይህንን የጥበብ ጌታ ለማወቅ ከፍ ያለ
ራብ ያድርበታል፡፡እናም ጌታውን በሚገባ እስኪያውቅና ነፍሱ በእውቀት እስትጥለቀለቅ ድረስ አይተኛም!
ጌታ ሆይ እንድናውቅህ እርዳን!!
መዝጊያ ጥቅስ ፡-
“ሰማያት
የእግዚአብሔርን ክብር ይናገራሉ፥
የሰማይም ጠፈር
የእጁን ሥራ
ያወራል። 2 ቀን ለቀን ነገርን ታወጣለች፥ ሌሊትም ለሌሊት እውቀትን ትናገራለች።ነገር የለም መናገርም የለም፥ ድምፃቸውም አይሰማም።ድምፃቸው ወደ ምድር ሁሉ፥ ቃላቸውም እስከ ዓለም ዳርቻ ወጣ።”
(መዝሙር 19፡1-4)