Friday, August 28, 2015

ልባሞች የሆናችሁ አይምሰላችሁ (ሮሜ 12፡16)

ይህን ቃል ጊዜ ሰጥታችሁ አስባችሁትና አሰላስላችሁት ታውቃላችሁ ? በዚህ ሳምንት ለእኔ የሚገርም ቃል ሆኖ ነው የከረመው፡፡እስቲ አስቡት፡፡አንዳንዴ ግሩም ስብከት ወይም ትምህርት ታስተምሩና፣አድናቆት የተቸረው ሥራ ታከናውኑና፣ስኬት የተጐናጸፈ ክንውን ትፈጽሙና፣ራሳችሁ ለራሳችሁ ፣ “እኔ ኮ ማን ይችለኛል፣ጎበዝ እኮ ነኝ ፤ማን ይበልጠኛል ?” ብላችሁ አታውቁም ?

በግሌ ልቤ የታበየበትና እራሴን ያሞካሸሁበት ብዙ ጊዜያት እንደ ነበሩ አልደብቃችሁም፡፡ብዙዎቻችን ጌታ ማስተዋል ካልሰጠን ለጌታ ልንሰጥ የሚገባውን ምሥጋናና ክብር ሊያሳንስ የሚችል አላዋቂነት አይጠፋንም ብዬ አስባለሁ፡፡ከዚህ ስህተት ጌታ ይጠብቀን! የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ብሎ አስረግጦ ይናገራልና፡-“ያልተቀበልኸው ምን አለህ ? የተቀበልህ ከሆነ ግን እንዳልተቀበልህ የምትመካ ስለ ምንድን ነው ?” (1 ቆሮንቶስ 4፡7)

ወገኖቼ እስቲ ደጋግማችሁ አስቡት፡፡እስቲ ምንድን ነው ያልተቀበልነው? የራሳችን የምንለው ነገር የቱ ነው ? መጠቀሚያ ዕቃዎች ነንና! በቃ ይኸው ነን፡፡ስለዚህ እጅግ ልናስተውል ይገባል፡፡የእግዚአብሔር ቃል “እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማል፤ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል” (ያዕቆብ 4፡6) ይላልና ሁልጊዜ አመለካከታችን በትሕትና መቃኘት ይኖርበታል ብዬ አምናለሁ፡፡ምክንያቱም እግዚአብሔር በምሕረቱና በረድኤቱ በሚታመኑ ነውና ደስ የሚሰኘው፤የሚደገፉበትን ይረዳል፣ይደግፋልም፡፡

በራሳችን፣በዕውቀታችንና በማናቸውም ምድራዊ ነገሮች መደገፍና ትምክህት አይጠቅመንም፣ይጐዳናል እንጂ፡፡የሚመካ ሰው ለሚታመኑበት አስተማማኝ በሆነው የፍቅር አምላክ ነው ሊመካ የሚገባው፡፡ቃሉ እንዲህ ብሎናልና፡-

“ጠቢብ በጥበቡ አይመካ፣ኃያልም በኃይሉ አይመካ፣ባለ ጠጋም በብልጥግናው አይመካ፤ነገር ግን የሚመካው። ምሕረትንና ፍርድን ጽድቅንም በምድር ላይ የማደርግ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን በማወቁና በማስተዋሉ በዚህ ይመካ፤ ደስ የሚያሰኙኝ እነዚህ ናቸውና፣ይላል እግዚአብሔር” (ኤርምያስ 9፡23-24)

ደግሜ እላለሁ፣ልባሞች የሆንን አይምሰለን፡፡ያለ እሱ ፈቃድ፣ድጋፍና ረድኤት፣ከፊታችን ተዘጋጅቶ የቀረበውን እንጀራ ቆርሶ ወደ አፍ ማድረግ እንኳ ከባድ ነው፡፡ስለዚህ ሁሌም በትሕትናና በምስጋና መንፈስ በፊቱ እንሁን፡፡የተደረገልን ነገሮች በመንፈስ እያየን እናክብረው፣ከፍ እናድርገው፡፡ተባረክ እንበለው፤በዚህ ደስ ይሰኛልና!

Sunday, August 23, 2015

Notice

 
To all my followers.I am living in Gaithersburg,Maryland.I wrote three books in Amharic.The first one is my autobiography,the second one is a collection of 75 poems and the third one is on The Benefits of Prayer.The books are very cheap and affordable.So,you can contact me with the following ways.
My phone :2403305004
My email :beke_abay@yahoo.com
I can be contacted thru facebook
Be blessed

Wednesday, August 19, 2015

yegizewkal.org

የእግዚአብሔርን እንጂ የሰው አናስብ


በማቴዎስ ምዕራፍ 16፣ጌታችን ኢየሱስ “ብዙ መከራ ይቀበል…..እንዲገባው” (ቁ.11) ለደቀ መዛሙርቱ በነገራቸው ጊዜ፣ጴጥሮስ ወደ ነበረበት ጠጋ ብሎ “አይሁንብህ ጌታ ሆይ ይህ አይደርስብህም”(ቁ.22) ብሎት ነበር፡፡ጌታ ኢየሱስም ወዲያው “ወደ ኋላዬ ሂድ አንተ ሰይጣን የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብምና ዕንቅፋት ሆነህብኛል” (ቁ.23)ብሎ ገሥጾታል፡፡

አዎ፣ጴጥሮስ በዛ ጊዜ የእግዚአብሔርን አልነበረም ያሰበውና ያደረገው፡፡ቢሆንም ከኢየሱስ ትንሣኤ በኋላና ታላቁን ተልዕኮ ተቀብለው ከተሰማሩ በኋላ፣ብዙ መከራን ተቀብሎ ያለፈ ትልቅ ሐዋርያና የእምነት ጀግና እንደ ነበር ታሪክና መጽሐፍ ቅዱስ ዘክረውታል፡፡ይህ ሐዋርያ የክርስቶስን መከራ በመካፈል ዙሪያ ጠንካራ መልእክቶችን መጻፉም ይታወቃል፡፡ከነዚህ መልእክቶቹ በሁለት ክፍሎች ላይ እንዲህ ብሏል፡-

“ወዳጆች ሆይ በእናንተ መካከል እንደ እሳት ሊፈትናችሁ ስለሚሆነው መከራ ድንቅ ነገር እንደ መጣባችሁ አትደነቁ፤ነገር ግን ክብሩ ሲገለጽ ደግሞ ሐሤት እያደረጋችሁ ደስ እንዲላችሁ በክርስቶስ መከራ በምትካፈሉበት ልክ ደስ ይበላችሁ”(1የጴጥሮስ 4፡12-13)

“በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዘላለም ክብሩ የጠራችሁ የጸጋ ሁሉ አምላክ ለጥቂት ጊዜ መከራ ከተቀበላችሁ በኋላ ፍጸማን ያደርጋችኋል፣ያጸናችኋል፣ያበረታችኋል”(1ጴጥሮስ 5፡10)

ልብ በሉ፤እነዚህን ጠንካራ መልእክቶች “አይሁንብህና አይድረስብህ” ያለው ጴጥሮስ ነው የጻፋቸው፡፡አይገርምም! በበኩሌ ሁሌ እነዚህን መልእክቶች ባነበብኩና ባሰላሰልኩኝ ቁጥር ይህንን ሰው ያገኘው ለውጥ ይደንቀኛል፡፡እንዲህ ሊል የቻለበት ምን ዓይነት ጥልቅ መንፈሳዊ ለውጥና መረዳት እንዳገኘው ገና በሚገባ ጥርት ብሎ አልገባኝም፡፡ነገር ግን ከጌታው ጋር የነበረው እጅግ የተጣበቀ ሕይወት ይኼንን ድፍረትና ትምክህት እንዳመጣለት አልጠራጠርም፡፡

ጌታ ኢየሱስ ጴጥሮስን ከገሠጸው በኋላ አስተሳሰባቸውንና አመለካከታቸውን ለማስተካከል ይመስላል፣ወዲያውኑ የክርስትያኖች ዋና ማገር የሆነውነንና ዘመን የማይሽረውን መልእክት የሰጣቸው፡፡መልእክቱ እንዲህ የሚል ነው፡-

“እኔን መከተል የሚወደ ቢኖር ራሱን ይካድ፤መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ፡፡ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ሁሉ ያጠፋታል፤ስለ እኔ ግን ነፍሱን የሚያጠፋ ሁሉ ያገኛታል”(ማቴዎስ 16፡22)

በዚህ ዘመን በዚህ ቃል ዙሪያ ብዙ ስብከትና ትምህርት እምብዛም አይሰማም፡፡ዛሬ ላይ የምንገኝ አማኞች(ብዙዎቻችን) በግብራችን እንደ ጴጥሮስ(ከመለወጡ በፊት) ዓይነት አመለካከትና አስተሳሰብ ያለን ይመስለኛል-“አይሁንብህና አይድረስብህ” የምንል፤የመስቀሉን መንገድ የምንሸሽ!
በፍጹም ዋጋ የሚያስከፍሉ፣ሕመም ያለባቸውንና መከራን የሚያመጡ ነገር ግን ክርስቶስ የሚከብርባቸውን ነገሮች አቋራጭ እየፈለግን እየሸሸንና እያመለጥን ያለን ይመስለኛል፡፡

ብዙዎቻችን በራስ ወዳድነት፣በስስትና በራስ ተኮር የኑሮ ዘይቤ ተጠላልፈን እራሳችኑኑ ስናስብና ስንከባከብ ነው ውለን የምናድረው(ምናልባት ተሳስቼ ከሆነ ልታረም እችላለሁ)፡፡የሕይወት ዘይቤአችን ይህንን ያለ ምንም ችግር የሚያሳብቅም ይመስለኛል፡፡እውነተኛና የምር የሆነ የክርስትና ሕይወትና ሩጫ ግን ይህንን አካሄድ በፍጹም አያስተምርም፣አያደፋፍርም፡፡ሕይወቱ በሚገባ ይተግበር ከተባለ “ለሌሎች የመኖርና ለሌሎች የመቆረስ ሕይወት”፣እንዲሁም "የመስቀል መንገድ" መሆኑ ሊታወቅና ሊሰመርበት ይገባዋል፡፡

በነገራችን ላይ ይህ ጽሑፍ ሰዎችን ለመውቀስ ታስቦ ሳይሆን፣በዚህ ዙሪያ ያለንን አመለካከትና አስተሳሰብ እንድናርቅ ሊረዳን ይችላል ብሎ ከማሰብ የመነጨ እንደ ሆነ እንዲታሰብልኝ እፈልጋለሁ፡፡

ሕይወት በምርጫዎችና በፈተናዎች የተሞላች ናትና በመንገዳችን ላይ ኢየሱስ የሚከብርባቸው ለጊዜው ግን የሚያሳምሙን ብዙ ጉዳዮች ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ለምሳሌ በእነዚህ የፈጠራ ምሳሌዎቼ ላይ ብትገኙ ምን ታደርጋላችሁ?

• ሰው ታሞ በመኪናችሁ እንድታደርሱት ቢጠይቃችሁና የተጠራችሁበትና የማትቀሩበት ሠርግ ቢኖር
• በእጃችሁ ያላችሁ 200 ብር ብቻ ነው፡፡ነገር ግን ያንን 200 ብር እጅግ በጣም ለአንገብጋቢ የሕይወት ጉዳይ የሚፈልግ ወንድም አጠገባችሁ ቢኖር
• እጅግ ግሩም የሆነ ሰው ሁሉ ተጠራርቶ እየሄደበት ያለበት ኮንፈረስ ላይ ለመሄድ እያሰባችሁ፣የታመመና የእናንተ ጉብኝት የሚያስፈልገው ወንድም ቢኖር

እናንተ ከነዚህ የበለጡ ብዙ ምሳሌዎችን ልትጨምሩ ትችላላችሁ፡፡በእያንዳንዱ በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታዎች የምንወስዳቸው እንደ ጌታ ፈቃድ ያሉ ርምጃዎች ጌታችን እንዲከብርና እንዲታይ ያደርገዋል፡፡ጌታ ኢየሱስም “መስቀል መሸከም” ብሎ የሚናገረው ስለ እንደዚህ ዓይነት ተመሳሳይ ርምጃዎች ነው፡፡ቢያምም የራስን ምርጫዎች ለሱ ክብር መተው! ቢያምም ረጅሙንና ፈታኙን ጎዳና ከሱ ጋር ተስማምቶ መጠብጠብ!

ከላይ ከጠቀስኳቸው ፈተናዎች ጠንከር ያሉ ብዙ ፈታኝ መከራዎችና መንገላታቶች ሊመጡ ይችላሉ፡፡እነዚህ ክስተቶች በየትኛውም መንገድ ወደ እኛ ይምጡ ውስጣችንን የሚፈትሹ ለመሆናቸው ምንም ጥርጥር ሊገባን አይገባም፤ጌታ ላይ መደገፋችንንና አለመደገፋችንን ይመሰክራሉና፡፡

በእንደዚህ ዓይነት ጊዜያት ከጫናው የተነሣ ስፍራችንን ሳንለቅ፣በጌታ ፊት በመሆን፣ጸጋን በመለመንና ለሥጋችን የሚመቸውን አካሄድ ሳንመርጥ፣እንደ ጌታ ፈቃድ በመሄድ እሱን በሕይወታችን ማሳየት ትልቅ አስተዋይነት ነው፡፡ከዛ ፈተና ስንወጣም የሚኖረን ምስክርነት ጠንካራ ይሆናል፡፡

ሰይጣን ይህ እንዳይሆንና እንደ ጴጥሮስ ዓይነት ለስጋ የሚመቹ አቋራጮችን ያሳየናል፣ያቀርባልም፡፡ስለዚህ በመንፈስ እያስተዋልን፣ “ወደ ኋላዬ ሂድ አንተ ሰይጣን የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብም”(ማቴዎስ 16፡23) ልንለው ይገባል፡፡

ጌታ ይርዳን!
Bekele Belachew
Write a comment...

Monday, August 17, 2015

አዲስ ራእይ ያስፈልገናል (Fresh vision)



ነቢዩ ኢሳይያስ በሱ ዘመን ከነበሩ የእግዚአብሔርን ሕግ በማወቅ በጽድቅና በቅድስና ከሄዱ ሰዎች መካከል አንዱ እንደ ነበር በጻፋቸው እጅግ በርከት ባሉት ትንቢታዊ መልእክቶቹ ላይ ይስተዋላል ፡፡

 
ነቢዩ ኢሳይያስ እግዚአብሔርን የሚፈራና የሚያውቅ ሰው በመሆኑ ከሱ ፈቃድ ባፈነገጠ ኑሮ የሚሄዱ እስራኤላውያንን ወደ መስመር እንዲገቡ ከበድ ያለ ተግሣጽ ያለው መልእክት ሲያስተላልፍ እንደ ነበረ የትንቢት ኢሳይያስ መጽሐፍ ከምዕራፍ አንድ እስከ አምስተኛ ምዕራፍ ያሉት ክፍሎችን ስናነብ እንገነዘባለን፡፡

 
ስካርን የሚከተሉትን፣አምላካቸውን የማያውቁትን፣ትዕቢተኞችን፣በደልን በምናምንቴ ገመድና ኃጢአትን በሠረገላ ማሠሪያ ወደ ራሳቸው የሚስቡትን፣ክፉውን መልካም እና መልካሙን ክፉ የሚሉትን፣በዓይናቸው ጥበበኞችና በነፍሳቸው አስተዋዮች የሆኑ የመሰላቸውን(ኢሳይያስ 5) ወዘተ ወዮላችሁ እያለ ሲያስጠነቅቅ ከርሞ፣በስድስተኛው ምዕራፍ ላይ ከዚህ በፊት አይቶት የማያውቀውን ከፍ ያለ አስደንጋጭ ራእይ አየ፡፡ጌታ እግዚአብሔር ራሱን በሚገርምና በሚያስፈራ መልኩ ገለጠለት፡፡ያ አስደናቂና አስደንጋጭ ራእይ፣ኢሳይያስን ወደ ራሱና ወደ ውስጥ እንዲመለከት አድርጐታል፡፡ክስተቱ እጅግ አስደንግጦት ነበርና፣እንዲህ ነበር ያለው፡-

 
“ከንፈሮቼ የረከሱብኝ ሰው በመሆኔ ከንፈሮቻቸውም በረከሱባቸው ሕዝብ መካከል በመቀመጤ ዓይኖቼ የሠራዊትን ጌታ ንጉሡን እግዚአብሔርን ስለ አዩ ጠፍቻለሁ ወዮልኝ” (ቁ.5)

 
ባጭሩ ወዮላችሁ ወደ ወዮልኝ ተቀየረ፡፡የሚገርም ነው፡፡በነገራችን ላይ “ጠፍቻለሁ” የሚለውን ቃል በእንግሊዝኛ መጽሐፍ ቅዱሶች ላይ ስመለከት “I am ruined” ወይም “I am undone” የሚሉ ትርጉሞችን እንደያዘ አይቻለሁ፡፡አር ሲ ስፕሮውል የሚባሉ የእግዚአብሔር ሰው ለዚህ ቃል ትክክለኛውና በጣም ተቀራራቢ የሆነው ትርጉም “I am undone” የሚለው እንደ ሆነ ባስተማሩት ትምህርታቸው ላይ ሰምቻለሁ፡፡ “ጠፍቻለሁ” የሚለው ቃል “አበቃልኝ አልተርፍም” እንደ ማለት ነውና፡፡
አዎ፣ነቢዩ ኢሳይያስ የነበረበት ሁኔታ የመጨረሻ የሚያርበተብት፣ግራ የሚያጋባና የሚያስጨንቅ ነበረ፡፡ከዚህም የተነሣ ይህ ነቢይ በብዙ ጥልቅ ንስሐ በጌታው ፊት ያሳለፈ ይመስለኛል፡፡እውነተኛ ጥልቅ ንስሐ ከባድ ነውና፣በብዙ ሕመም እንዳሳለፈ የሚጠቁመን ክፍል ቁ.6 ነው፡፡እንዲህ ይላል፡-

 
“ከሱራፌልም አንዱ እየበረረ ወደ እኔ መጣ፤በእጁም ከመሠዊያው በጉጠት የወሰደው ፍም ነበረ፡፡አፌንም ዳሰሰበት”(ቁ.6)

 
ከንፈራችን በጣም ስስና በቀላሉ የሚጐዳ የአካል ክፍላችን እንደ ሆነ ይታወቃል፡፡እዚሁ ክፍል ላይ ነው በጉጠት የነበረው ፍም ያረፈው፡፡እጅግ በጣም እንደሚያም መገመቱ ከባድ አይሆንም፡፡አዎ፣ይህ ሕመም ትክክለኛና እውነተኛ ንስሐ ዋዛ እንዳልሆነ ይጠቁማል፡፡በዚያ የጋለ ጉጠት ላይ በነበረው ፍም ከንፈሩ ከተዳሰሰ በኋላ ነበረ በደሉ የተሻረለት፤ኃጢአቱም የተሰረየለት(ቁ.7).ከዚያም “ማንን እልካለሁ? ማንስ ይሄድልናል?” (ቁ.8) ሲባል “እነሆኝ እኔን ላከኝ” ( ቁ.8) የሚል ትሕትና የተላበሰ ቋንቋ  ከአንደበቱ ወጣ፡፡


 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያየናቸው ነቢያትና ጸሐፍት ክብሩን አይተው ደንግጠውና ተለውጠው ቀርተዋል፡፡እውነት ለመናገር በበኩሌ “እባክህ ተገለጥና ትንሽ አስደንግጠን” የሚል ጸሎትም እየዳዳኝ ነው፡፡ሐዋርያው ዮሐንስ የጌታን ክብር ሲያይ “ባየሁትም ጊዜ እንደ ሞተ ሰው ሆኜ ከእግሩ በታች ወደቅሁ” (ዮሐንስ 1፡17)ብሎ ተናግሯል፡፡ነቢዩ ዳንኤል እግዚአብሔርን በክብሩ ሲያየው“ኃይልም አልቀረልኝም፤ደም ግባቴም ወደ ማሸብሸብ ተለወጠብኝ፤ኃይልም አጣሁ፡፡የቃሉንም ድምፅ ሰማሁ፤የቃሉንም ድምፅ በሰማሁ ጊዜ ደንግጬ በምድር ላይ በግምባሬ ተደፋሁ” (ዳንኤል 10፡8-9) ብሏል፡፡ነቢዩ ሕዝቅኤል ያንን አስገራሚ የእግዚአብሔር ክብር ምሳሌ ሲመለከት፣ “ባየሁም ጊዜ በግምባሬ ተደፋሁ”(ሕዝቅኤል 1፡28) ብሎ ነበር ክስተቱን የገለጸው፡፡ነቢዩ ዕንባቆ የእግዚአብሔር ክብር መምጣቱን በመንፈሱ አውቆ የተናገረው ነገር እጅግ ያስደንቀኛል፡፡እንዲህ ነበር ያለው፡-

 
“እኔ ሰምቻለሁ፣ልቤም ደነገጠብኝ፤ከድምፁ የተነሣ ከንፈሮቼ ተንቀጠቀጡ፤መንቀጥቀጥ ወደ አጥንቶቼ ውስጥ ገባ፤በስፍራዬ ሆኜ ተናወጥሁ” (ዕንባቆ 3፡16)

 
የእግዚአብሔር ሰማያዊ ጉብኝት አስደናቂም አስፈሪም ነው፡፡እኔ ሳስበው፣እግዚአብሔርን የተዳፈርንበትና ኃጢአትን አቅለን ያየንበት ምክንያት፣ጌታን በትክክል ስላልተረዳነውና በዚህ መልኩ(ትንሽም ቢሆን) በመንፈስ ሰላላየነው ይመስለኛል፡፡ታዲያ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል ? ብናየው ሁኔታዎች ይቀየራሉ የሚል እሳቤ አለኝ፡፡

 
የሚያገለግሉንና የሚያስተምሩን ሰዎች እግዚአብሔርን በእንደዚህ ዓይነቱ ሁኔታ (በትንሹም ቢሆን) ያላዩ ሰዎች ስለሆኑ፣ትክክለኛው የጌታችን ስዕል በብዙዎቻችን ዘንድ ጠፍቶብናል፡፡ስለዚህም እግዚአብሔርን መፍራት ከየት ይመጣል? ለዚህም ነው ብዙ ያገጠጡ ችግሮች በመካከላችን የሚታዩት፡፡

 
በግሌ በራሴ ሕይወት ደጋግሜ ማፈሬን አልደብቃችሁም፡፡እግዚአብሔርን እንደሚገባኝ አለመፍራቴን መንፈስ ቅዱስና ሕሊዬ ይመሰክሩልኛል፡፡የቅርብ ጊዜ ጸሎቴም እሱን በሚገባ መፍራት ወደ ሕይወቴ እንዲመጣ ነው፡፡ዋናውን ጥሎ ወደ የት ?

 
የእግዚአብሔርን ክብር ያዩ ሰዎች በሕይወታቸው ትልቅ ለውጥ እንደነበራቸው መጽሐፍ ቅዱስ በተለያዩ ቦታዎች ተርኮልናል፡፡ሐዋርያው ጳውሎስ በሚያስደነግጥና በሚያስገርም ጉብኝት ነበር ወደ ጌታው የተመለሰው(ሐ.ሥራ 9፡1-9)፡፡ለዚህም ነው “በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ መዳናችሁን ፈጽሙ”(ፊሊጵስዩስ 2፡12) ብሎ የመከረን፡፡

 
የእግዚአብሔር ቃል “ልጆቼ ኑ ስሙኝ እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችኋለሁ” (መዝሙር 34፡11) ይላል፡፡አዎ፣እግዚአብሔርን በመፍራትና በመንቀጥቀጥ ለማክበርና ለመገዛት፣ቀርበነው ከራሱ መማር ያስፈልገናል፡፡በጽኑ ጸሎት ፊቱን መፈለግ ይኖርብናል፡፡ከቃሉ ጋርም ጠንከር ያለ ቁርኝት ያስፈልገናል፡፡መንገዱ ይኸው ነው--ቀርቦ ማወቅ(relational knowledge)! ስለዚህ ጌታ አዲስ ራእይ፣አዲስ ዕይታ፣አዲስ ማስተዋልና አዲስ ምልከታ እንዲሰጠን ፊቱን እንፈልግ!
 

Friday, July 31, 2015

ከአደንዛዥ ዕፅ እሥራት የተፈታችው ጄሲ



ስሟ ጄሲ ይባላል፡፡አደንዛዥ ዕፅ ስትወስድ በትንሹ አትረካትም፡፡ዕፆቹን በተለያዩ መልኩ ትወስዳቸው ነበር፡፡የ 16 ዓመት ልጅ ሆና እናቷ ለጭንቀት የምትወስዳቸውን እንክብሎች እና አልኮሆል መውሰድ የጀመረችው፡፡

ከሕፃንነቷ ጀምራ በእንጀራ አባቷ ብዙ በደል ደርሶበታል፡፡ይህ ሰው እናቷንም በኃይል ያንገላታት ነበር፡፡ሰክሮ መጥቶ እናቷ ላይ ሽጉጡን ደግኖ ሲያስፈራራት የሚያመሽበት ጊዜ ጥቂት አልነበረም፡፡

እናቷ ከዚህ ሰው ጋር የጄሲ ዕድሜ ገና አሥራ ውስጥ ሆኖ ሳለ ነበር የተፋቱት፡፡ሰውየው ከቤታቸው ከሄደ በኋላም ቢሆን፣ጄሲ ውስጥ ገና ያልጠገገ ቁስል ነበር፡፡ታዲያ ሕመሟን ለማስታገስ ስትል አልኮሆል አብዝታ መጠጣቷን ተያያዘችው፡፡ካሳለፈችው መከራ የተነሣ ጠባይዋ የተበላሸ ነበርና ከብዙ ሰው ጋር ያጣላት ነበር፡፡

እናቷ የምትወስደውን ዛናክስ በመዋጥና አልኮሆል በመጠጣት ራሷን ማደንዘዟን ቀጠለች፡፡ከዚያም ከበድ ወዳለ ሜት ወደሚባል መድኃኒት ዞረች፡፡ስለምንም ነገር ማሰብ አቁማ ነበር፡፡ባጭሩ ግዴለሽነት የተጠናወተው ሕይወት መግፋት ዕጣ ፈንታዋ ሆነ፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ አረገዘችና ወንድ ልጅ ወለደች፡፡ከዚህ በኋላ ለልጄ እኖራለሁ ብላ ለራሷ ቃል ኪዳን ገባች፡፡ቢሆንም እንደዚያ መሆን አልቻለችም፡፡ከዚያም ሁለተኛ ወንድ ልጅ ደገመች፡፡ሕይወቷ የበለጠ ተወሳሰበ፡፡ስለዚህ የበለጠ ተዝረከረች፡፡

ጄሲ የምትወስደውን የሜት መጠን ስለ ጨመረችው፣ሕይወቷን ተቆጣጠረው፡፡የበለጠ ሕይወቷ እንደ ዓይን ጠፋ፡፡አብሯት ይኖር የነበረው ጓደኛዋ አካሄዷን ዓይቶ ጥሏት ሄደ፡፡መንግሥት ልጆቹን ከሷ ነጥቆ እሱ እንዲያሳድግ አደራ ጣለበት፡፡

ሕይወቷ ከመበላሸቱ የተነሣ አጠገቧ የሚሆንና የሚያጽናናት ምንም ነገር አልነበረም፡፡ጓደኞቿ ትተዋታል፤ልጆቿም ከሷ ጋር የሉም፤ልቅሶ ብቻ!ከዚህም የተነሣ ጄሲ ሕይወቷ በኃይል አስደንገጣት፡፡ያለችበት የቁልቁለት መንገድ አንድ ቦታ ላይ መቆም እንዳለበት አሰበች፡፡

በዚህ አጋጣሚ እናቷ ጌታ ኢየሱስን መከተል ጀምራ ሕይወቷ ሰመረና በኃይል ተለወጠች፡፡ስለዚህ ጄሲን ደጋግማ ቤተ ክርስትያን እንድትሄድ ትጋብዛትና ትመክራት ጀመር፡፡የእናትየው ንዝነዛ ፍሬ አፈራና ጄሲ ሰክራም ቢሆን መሄድ ጀመረች፡፡እቤት በምትቆይበት ሰዓት ደግሞ ወደ አምላኳ አብዝታ መጮኽ ጀመረች፡፡ብዙ ሳይቆይ ጸሎቷ ተሰማና፣በሕይወቷ ተለማምዳው የማታውቃው ሰላም አጥለቀለቃት፡፡የሱስ እስራቶቿ ተበጣጥሰው ነፃ አየር መተንፈስ ጀመረች፡፡

ለውጡ እጀግ ደስ ስላሰኛት ሕይወቷን ሙሉ በሙሉ ለጌታዋ ለኢየሱስ አስረከበች፡፡ከዚያማ የመጀመሪያ ያደረገችው ነገር፣አብሯት ይኖር የነበረውንና የሁለት ልጆች አባት ጓደኛዋ ጋር መደወል ነበር፡፡ባለቤቷ መለወጧን ሲሰማ እጅግ ደስ አለው፡፡ከዚያም አብረው እንዲኖሩ ያቀረበችለትን ሐሳብ በደስታ ተቀብሎ አብረው መኖር ጀመሩ፡፡ድል ባለ ድግስም ተጋቡ፡፡

ዛሬ ጌታ አንድ ሴት ልጅ ጨምሮ ባርኳቸው፣አምስት ሆነው ባንድ ጣራ ስር አብረው በደስታ ይኖራሉ፡፡ ጄሲ ስትመሰክር “ሰዎች በዚህ ዘመን እግዚአብሔር ተዓምር አይሠራም እያሉ ሲያወሩ እሰማለሁ፡፡ኧረ ለመሆኑ ከዚህ በላይ ተዓምር ምንድነው?”

http://www.cbn.com/700club/features/amazing/

Thursday, July 30, 2015

እነዚህ የደረቁ አጥንቶች በሕይወት ይኖራሉን?




 መንገድ ላይ እየሄድሁ ሳለ ድንገት “እነዚህ የደረቁ አጥንቶች በሕይወት ይኖራሉን?” የሚል መንፈሳዊ ድምፅ ወደ ውስጤ ዘልቆ እያሰብኩ የነበረውን ነገር አቋረጠኝ፡፡ጥያቄውን በውስጤ እንደሰማሁት ወዲያው ግርታና ግርምት እንደ ነበረኝ አልደብቃችሁም፡፡አሁን ግን በከፊልም ቢሆን የመጣው መልእክት ያለ ምክንያት አልመጣም ብዬ ስለማስብ ደስታን ፈጥሮብኛል፤ምንም እንኳ ጥያቄው እንዴት እንደሚመለስ ባላውቅም፡፡


እግዚአብሔርን ከኃያላኖች በላይና ልዩ የሚያደርገው የትንሣኤ አምላክ መሆኑ ነው፡፡አልቻልና አልታለፍ ያለውን ነገር ያስችላል፣ያሳልፋልም፡፡የከበደን ጉም ገፎ ደህና የሆነ ዘመንን ያመጣል፡፡ይህ ደግሞ በብዙዎች ዘንድ የተመሰከረ ነው፡፡የእስራኤል በ1948 መንግሥቷ ከፈራረሰና ከባዶ ነገር እውን ሆኖ መመለሱ አንዱ የዓለማችን ትንግርትና ይህንኑ የሚመሰክር ክስተት ነው፡፡
መቼም ስለ “የደረቁ አጥንቶች በሕይወት መኖር” ሳስብ የራሴ ሕይወት ነው ቶሎ ወደ አእምሮዬ የሚመጣው፡፡ተስፋ እንደሌለው፣ነፍስ ሊዘራ እንደማይችልና እንደ “ደረቀ አጥንት” ሕይወቴ ትርጉም አጥቶ የነበረበትን ዘመን አስታውሳለሁ፡፡በፍጹም ይሄ ዘመን ይመጣል ብዬ በሕልሜም ሆነ በውኔ አስቤ አላውቅም፡፡ያሳለፍኩት ጉስቁልና በዝርዝር ይተረክ ቢባል አንድ መጽሐፍ ብቻ የሚበቃው አይመስለኝም፡፡በዚያ የጨለማ ወቅት ብዙ ተስፋ መቁረጥ ነበር፤አንገት ማቀርቀር ነበር፤መሸማቀቅ ነበር፤ጭንቀትና ኀዘንም የማይለዩኝ የዘወትር ዕጣ ፈንታዎቼ ነበሩ፡፡እግዚአብሔር ይህንን በሁሉ መልኩ የሞተና ሙሉ በሙሉ የወደቀ ሕይወት ነው ትንሣኤ ሰጥቶ ይችን መልእክት ለምስክርነት የምጽፍላችሁ፡፡


መጽሐፍ ቅዱስን ሳነብ ከምደነቅባቸው ክፍሎች ሕዝቅኤል ምዕራፍ 37 ዋነኛው ነው፡፡ምክንያቱም ግልጽ ነው-ትንሣኤን ያውራልና ነው! ነቢዩ ሕዝቅኤል እንዲህ ብሎ ይናገራል፡-


“እግዚአብሔርም በመንፈሱ አወጣኝ፣አጥንቶችም በሞሉባት ሸለቆ መካከል አኖረኝ….በዙሪያቸው አሳለፈኝ፡፡እነሆም በሸለቆው ፊት እጅግ ብዙ ነበሩ፤እነሆም እጅግ ደርቀው ነበር” (ቁ.2)


ይህ ትንቢታዊ መልእክት የተጻፈው በምንም ተዓምር የኛ ነገር አበቃ ስላሉና በቃ አለቀልን ከዚህ በኋላ ትንሣኤ አናያም ብለው የደመደሙ እስራኤላውያንን አስመልክቶ ነው፡፡የነበሩበት የግዞትና የልቅሶ ጊዜ አንገሽግሿቸው በነበረበት ጊዜ የመጣ ትንቢት ነው፡፡ለመሆኑ ያንን ሁኔታና ጊዜ ዐይቶ ማንስ ትንሣኤን ያስባል ? በዚያን ጊዜ እነዚህ እስራኤላውያን “አጥንቶቻችን ደርቀዋል፣ተስፋችንም ጠፍቶአል፣ፈጸመንም ተቈጠርናል” (ቁ.11)ብለው ነበር፡፡ነገር ግን የመጣው ትንቢታዊ መልእክት እጅግ ተቃራኒ ነበር-ትንሣኤ(ቁ 12-14)!


አዎ፣ተስፋ መቁረጥ፣ፈጽሞ መውደቅ፣የኑሮ ትርጉም ማጣትና የሕይወት መድረቅ የሚያጋጥሙ ክስተቶች ናቸው፡፡አዎ፣የባዶነት ጊዜያትና የጭንቀት ጊዜያት ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ሕይወት እንደ “ደረቁ አጥንቶች” ትንሣኤ የሌለው እስኪመስል ድረስ፣ጣዕም የሌለው እስኪመስል ድረስ ጣዕም ሊያጣ ይችላል፡፡ቢሆንም ዋናው ቁም ነገር በዚህ ጊዜ ምን እናድርግ የሚለው ነው ትልቅ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው፡፡


በዚህ ጊዜ ከምንም ጊዜ በላይ ወደ ጌታ አብዝቶ መጮኽና በፊቱ መሆን ያስፈልጋል(ለጊዜው ትርጉም ባይሰጥ እንኳን)፡፡የምሕረት አምላክ በደረቁ ነገሮቻችን ላይ ልምላሜና ትንሣኤ እስከሚያመጣ ድረስ በፊቱ መውደቅ ተፎካካሪ የሌለው ምርጫ ነው፡፡ነፍስን ሊያለመልም፣ሊያጽናና ሊያንጽ የሚችለውንና ልብን የሚያቀናውን ቃል በተጓዳኝ እያሰላሰሉ በፊቱ መሆን አስተዋይነት ነው ብዬ)አስባለሁ፡፡አዘውትሮ መጾም በግሩም ሁኔታ ሕይወትን ሲደግፍና በጌታ ላይ ያለን መጣበቅ ሲጨመር አይቼዋለሁና አዘውትሮ መለማመዱ ግሩም ነው ብዬ እመክራለሁ(ኢሳይያስ 58)፡፡


በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ ሆነን እየተጋን ስንጠባበቀው፣የፍቅር ጌታ በራሱ ሰዓት ሊያስደንቀንና ሊጎበኘን

  •     በድምፁ ይመጣል
  • ምሕረቱን ይገልጣል

  • በተዓምሩና በክብሩ በደረቁ ነገሮቻችን ላይ ይገለጣል

እናም  “የደረቁ አጥንቶች በሕይወት ይኖራሉ”(ቁ.6)


ስሙ ለዘላለም ይባረክ!

Wednesday, July 22, 2015

ባለ ብዙ ማስረጃ ሕይወት



ባለ ብዙ ማስረጃ ሕይወት

ሰሞኑን መጽሐፍ ቅዱስን ሳነብ የኢየሱስ ደቀ መዛሙርት የነበሩትን፣ሐዋርያት ሆነው የተመረጡትን የጴጥሮስን፣የጳውሎስንና የሌሎችንም ምሥክርነት እያነበብኩ ልቤ በደስታ እየፈነጠዘ ሐሤት አደርግ ነበር፡፡እኒህ አባቶች በቀጥታ ከራሱ የሰሙትንና ከርሱ ጋር በነበራቸው ትስስር የዳሰሱትንና ያዩትን ነው የጻፉልን፡፡እነዚያን ማስረጃዎች በጥልቅ ብናስተውል መንፈሳዊ ሕይወታችን በኃይል ይለወጣል ብዬ አስባለሁ፡፡እኒያ ሐዋርያት ያለ ምንም መካከለኛ ተቀባይና ተላላኪ ነው ከኢየሱስ ከራሱ በቀጥታ የተቀበሉትን የነገሩን፡፡ይሄ መቼም የሚደንቅ ነገር ነው፡፡እስቲ አንዳንድ ያስደነቁኝን ጥቂት ነገሮች ላካፍላችሁ፡፡


የእግዚአብሔር ቃል ኢየሱስ ከትንሣኤው በኋላ “አርባ ቀን እየታያቸው፣ስለ እግዚአብሔርም መንግሥት እየነገራቸው በብዙ ማስረጃ ከሕማማቱ በኋላ ሕያው ሆኖ ለእነርሱ አሳያቸው”(ሐዋ.ሥራ 1፡3፤አጽንኦት በእኔ የተጨመረ)፡፡እስቲ አርባ ቀን የሚለውንና በብዙ ማስረጃ የሚለውን በልባችሁ አስምሩልኝ፡፡አይደንቅም? አንድ ቀን ወይም ለጥቂት ጊዜ አይደለም የታያቸው-አርባ ቀን !ደግሞም በብዙ ማስረጃ ነው የታያቸው፡፡በግሌ የዛሬ 16 ዓመት ገደማ፣ለደቂቃዎች በራዕይ ዐይቼው ተደንቄ ቀርቻለሁ፡፡ይገርማል እነዚህን ድንቅዬ ተደጋግመው ቢነበቡ የማይሰለቹ ማስረጃዎችና ልምምዳቸውን ነው በወንጌላት የጻፉልን፡፡
ከሚደንቀኝ ምንባብ ውስጥ ሌላውን እነሆ(ሐዋርያው ጴጥሮስ ስለ ኢየሱስ ሲመሰክር የተናገረውን ነው)፡-


“እኛም በአይሁድ አገርና በኢየሩሳሌም ባደረገው ነገር ሁሉ ምስክሮች ነን እርሱንም በእንጨት ላይ ሰቅለው ገደሉት።እርሱን እግዚአብሔር በሦስተኛው ቀን አስነሣው ይገለጥም ዘንድ ሰጠው፤ ይኸውም ለሕዝብ ሁሉ አይደለም ነገር ግን በእግዚአብሔር አስቀድሞ የተመረጡ ምስክሮች ለሆንን ለእኛ ነው እንጂ፤ ከሙታንም ከተነሣ በኋላ ከእርሱ ጋር የበላን የጠጣንም እኛ ነን።ለሕዝብም እንድንሰብክና በሕያዋንና በሙታን ሊፈርድ በእግዚአብሔር የተወሰነ እርሱ እንደ ሆነ እንመሰክር ዘንድ አዘዘን”(ሐዋ.ሥራ 10፡39-42))

 
አዎ፣ከትንሣኤው በኋላ አብረውት አሳልፈዋል፡፡አብረውት በልተዋል፣ጠጥተዋልም፡፡ከአፉም ድንቅ የሆነውን ልብን በመለወጥ የሚታወቀውን ቃሉን ተቀብለዋል፡፡ያንን ደግሞ ለእኛ አስተላልፈውት በሕይወታችን ድንቅ ሥራን እየሠራ ይገኛል፡፡ኢየሱስ ሦስቱ ሐዋርያትን(ጴጥሮስን፣ያዕቆብንና ዮሐንስን)ብቻቸውን ወደ ረጅም ተራራ ካወጣቸው በኋላ በፊታቸውም ተለውጦ ክብሩን ዐይተዋል(ማቴዎስ 17፡1-2 ያነቧል)፡፡ይህንን ክስተት ሐዋርያው ጴጥሮስ በመጥቀስ፣የተሰጠን ወንጌል በእውነተኛ ምስክሮች ላይ የተደላደለ እንደ ሆነ እንዲህ ብሎ መስክሯል(እኔ መቼም ይህንን ክፍል ስለምወደው ደጋግሜ ነው የማነበው)፡-


“ከገናናው ክብር በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው የሚል ድምፅ በመጣለት ጊዜ ከእግዚአብሔር አብ ክብርንና ምስጋናን ተቀብሎአልና፤እኛም በቅዱሱ ተራራ ከእርሱ ጋር ሳለን ይህን ድምፅ ከሰማይ ሲወርድ ሰማን።ከእርሱም ይልቅ እጅግ የጸና የትንቢት ቃል አለን” (2 ጴጥሮስ 1፡16-19)


ይሄ አስደናቂ መልእክት ነው፡፡ከሰማይ የመጣውን ድምፅ በቀጥታ ነበር የሰሙት፡፡ጌታ ዐይኖቻችንን ከፍቶ ይህንን መልእክት ብናየውና ብንረዳው እጅግ ሕይወትን የሚለውጥ ምስክርነት ሆኖ እናገኘዋለን፤ሐዋርያው እንደ ወረደ የተቀበለውን ነውና የሰጠን! ደግሞም ያየነውና የዳሰስነው ብቻ በቂ አይደለም ይለናል፤ “ከእርሱም ይልቅ እጅግ የጸና የትንቢት ቃል አለን’’ ነው የሚለን-የማይናወጥ፣የማይሰበር፣የማይታጠፍ፣የማይለወጥ፣ሰባት ጊዜ እንደ ተጣራ ብር የነጠረ!


ሐዋርያው ዮሐንስም በግልጽ በሚገባን አገላለጽ እንዲህ ብሎ ነግሮናል(ይኼን ክፍልማ ሳነበው እጅግ ነው የሚገርመኝ፤ደጋግሜ አንብቤው አልጠግብም)፡-


“ስለ ሕይወት ቃል ከመጀመሪያው የነበረውንና የሰማነውን፣በዓይኖቻችን ያየነውን፣የተመለከትነውንም፣እጆቻችንም የዳሰሱትን እናወራለን፤ሕይወትም ተገለጠ አይተንማል፣እንመሰክርማለን፤ከአብ ዘንድ የነበረውንም ለእኛም የተገለጠውን የዘላለምን ሕይወት እናወራላችኋለን”(ዮሐንስ 1፡1-2)


በዚህ ምንባብ ያሉትን አገላለጾች እስቲ ሰከን ባለ ሁኔታ አስቧቸው፤ልብ ነው የሚንጡት-ያየነውን፣የተመለከትነውን፣የዳሰስነውን፣ለእኛም የተገለጠውን!! ቢሆንም እግዚአብሔር አምላክ በእነዚህ በምናነባቸው የጸኑ ምስክሮች ብቻ አልተወንም፡፡በተግባር ደረጃ ራሱን በተለያየ መንገድ እየገለጠ አሳይቶናል፡፡ሲደግፈን፣በመከራ ውስጥ ጸጋ ሰጥቶ ሲያሳልፈን፣ልባችንን በመንፈሱ ኃይል በደስታና በሐሤት ሲያሞቀውና አንችልም ያልነውን እንድናልፍ እያደረገ ቀጥተኛ የሆነ ምስክረነት በልባችን እየጻፈ ይገኛል፡፡ብርሃኑን በልባችን ያበራ እግዚአብሔር ስሙ ለዘላለም ይባረክ!!


Wednesday, July 8, 2015

በአንዲት ውብ ዝማሬ ከሞት ያመለጠው ጄምስ



ጄምስ ዊልፎንግ እናቱ በጣም የሚወደውን ወላጅ አባቱን መግደሏን ገና እንቦቀቅላ ሕጻን ሆኖ ነው የሰማው፡፡ጄምስ ሲናገር “ከቤት ልወጣ ልብሴን እያዘጋጀሁ ነበር፡፡ድንገት እናቴ ቀልቧን ስታ ነው መሰል ሽጉጧን አንሥታ አባቴ ላይ አንድ አገር ጥይት አርከፍክፋ የገደለችው” ብሎ መስክሯል፡፡

ጄምስ ያባቱን አስደንጋጭ ዜና ሲሰማ የነበረውን ሁኔታ በሚገባ ያስታውሰዋል፡፡ያ ሁኔታ በአእምሮው ላይ ትልቅ ቁስል ጥሎበትም አልፏል፡፡በተጨማሪም የዘጠኝ ዓመት ልጅ ሳለ፣በቅርብ ቤተ ዘመዱ ተደጋግሞ ተደፍሯል፡፡ምስጢሩን ካወጣ ሰውየው ሊገድለው እንደሚችል አስጠንቅቆታልና፣ለ 42 ዓመታት ለማንም ተንፍሶት አያውቅም፡፡

ይህ ሁኔታ ጄምስ ለእግዚአብሔርና ለሰዎች ያለውን ስዕል አበላሽቶበታል፡፡የሁልጊዜም ጥያቄው “እግዚአብሔር ካለ ለምን እንዲህ እንድሆን ፈቀደ ?” የሚል ነበር፡፡አባቱ ስለሞተና እናቱ ወደ ወኅኒ ስለ ወረደች፣ጄምስ እና ወንድሞቹ ወደ ሕጻናት ማሳደጊያ ተላኩ፡፡ነገር ግን ብዙ ሳይቆይ፣ጄምስ በሕጻናት ማሳደጊያው የጠበቀውን ክብካቤ ስላላገኘ ኮበለለ፡፡

ከማሳደጊያው ከኮበለለ በኋላ፣ስለ ምንም ማሰብ አቆመ፡፡ራሱንም ለመግደል በርካታ የሕክምና እንክብሎችን ወስዶ ታሞ ነበርና፣ ሆስፒታል ውስጥ ትንሽ ጊዜ ተኝቷል፡፡ከሆስፒታል ከወጣ በኋላ ጎዳና ላይ መኖሩን ተያያዘው፡፡ከዚያማ የአደንዛዥ ዕፅና የአልኮሆል ሱሰኛ ሆነ፡፡ይህንን ያደረገው የውስጥ ሕመሙን ለመርሳት ነበር፤ባሰበት እንጂ!

ጄምስ ባሪያ ያደረገውን ሱሱን ለማስተናገድና በገንዘብ ለመደገፍ ሲል፣ቤት ውስጥ እየገባ መዝረፍ ጀመረ፡፡ከዝርፊያው ጋር በተያያዘ ሁለት ዓመት ታሰረና ተፈታ፡፡ለሁለተኛ ጊዜ ለ 14 ዓመት ተፈረደበትና ታሰረ፡፡የእስር ጊዜውን ጨርሶ ከወጣም በኋላ በኑሮው ዘይቤው ምንም ለውጥ አልነበረውም፡፡

ጄምስ ይባስ ብሎ የኮኬይን ጥገኛ  ሆነ፡፡የአልኮሆል አጠጣጡም ከወትሮው እየጨመረ መጣ፡፡አንድ ቀን ለ 48 ሰዓታት ኮኬይንና አልኮሆል ደባልቆ ወስዶ ሲነቃ በኃይል አሞት ነበርና እጅግ መረረው፡፡በዚያ ብሶት እግዚአብሔርን “እንዲህ ሆኜ ወደ ፊት መቀጠል አልፈልግም፡፡አንተ በውኑ እንደሚባለው ትልቅ ከሆንክ፣ለምን በእንደዚህ ዓይነት ሕይወት እንድቀጥል ፈቀድህ?” ብሎ ይጠይቃል፡፡ከዚያም ሽጉጡን አንሥቶና ጭንቅላቱ ላይ ደቅኖ ለመተኮስ ቢሞክር አልሠራ ይለዋል፡፡ከዚያ በኋላ “ራሴን ሌላ ሙከራ አላደርግም” ብሎ ለራሱ ይምላል፡፡

አንድ ቀን ጄምስ የሚሠራበትን የመሥሪያ ቤት ወለል እያጸዳ ሳለ፣የሥራ ባልደረባው “ኢየሱስ ይወደኛል” የሚል መዝሙር ሲዘምር ይሰማዋል፡፡ከዚያም ባልደረባውን “እንዴት ኢየሱስ ይወደኛል? እስቲ ተመልከት፣ሕጻን ሳለሁ በአዋቂ ቤተ ዘመድ ተደፍሬአለሁ፤እናቴ የምወደውን ወላጅ አባቴን በጥይት ገደለችው፡፡ራሴን ለመግደል ብዙ ሞክሬአለሁ፤ጥሩ ሕይወት ኖሬ አላውቅም፡፡ዘራፊና ወንበዴ ነበርሁ፡፡ኢየሱስ ይወድሃል ነው የምትለኝ? እንዴት ሊወደኝ ይችላል? ብሎ ይጠይቀዋል፡፡

ባልደረባውም በጥሩ ሁኔታ ጥያቄውን ስለመለሰለት፣ልቡ በግሩም ሁኔታ ይነካል፡፡ከዚያም ቤቱ ሄዶ ጮክ ብሎ “እግዚአብሔር ሆይ ከወደድከኝ እባክህ ወደ ሕይወቴ ና፤ኃጢአቴን ሁሉ ይቅር በለኝ” ብሎ ይጸልያል፡፡ልክ ያንን ጸሎት ከጸለየ በኋላ እላዩ ላይ የነበረው ሸክም ሁሉ እንደተራገፈ ተሰማው፡፡ክንፎች ያሉትና መብረር የሚችል ያህል ነበር ስሜቱ፡፡ከዚያም መጽሐፍ ቅዱስን ያለማሰለስ ማጥናቱን ተያያዘው፡፡ከጥቂናት በኋላ መሥሪያ ቤት ያዩት ሰዎች ለውጡን ዐይተው ሲጠይቁት “ኢየሱስን አገኘሁት፤ድኛለሁ” ይላቸዋል፡፡

ከዚያም ጄምስ የውስጥ ሕመሙ ሙሉ በሙሉ ይድን ዘንድ የበደሉትን መማር እንዳለበት ተረድቶ ነበርና፣ሕጻን ሳለ ክፉኛ የበደለውን ዘመዱን ስልክ ደውሎ “ምሬሃለሁ” አለው፡፡በተጨማሪም አብራው አንድ ቤተ ክርስትያን የምታመልከውን እናቱን በሙሉ እንደማራት ነገራት፡፡በዚህ ሰዓት ባንድ ቤተ ክርስትያን በፓስተርነት ያገለግላል፡፡ግሩም የሆነ ትዳርም ይዟል፡፡

ጄምስ “ወደ ኋላ ሳስበውና የአሁኑን ሕይወቴን ሳስተያየው፣ይህንን ያለሁበትን ለውጥ ከጌታ በቀር ማንም ሊያደርግ እንደማይችል እመሰክራለሁ” ብሏል፡፡በተጨማሪም “ሕይወቴን በ1997 ዓ.ም ለጌታ ሳስረክብ፣ውስጤን የቀየረ ብርሃን ወደ ልቤ ገብቷል፤ስሙ ለዘላለም ይባረክ” ብሎ መስክሯል፡፡

አዎ፣እውነት ነው! ጌታ ኢየሱስን የመሰለ አዳኝና ምስኪንን ከፋንድያ ማንሣት የሚችል ብቃትና ችሎታ ያለው አምላክ አላየንምና ስሙ ከዘላለም እስከ ዘላለም ይባረክ!!