Tuesday, May 20, 2014
የጸሎት ሦስቱ ሂደቶች
የጸሎት ሦስቱ ሂደቶች
1. “ነፍሴ አንተን ተጠማች” (መዝሙር 63፡1)
2. “ነፍሴ በኋላህ ተከታተለች” (መዝሙር 63፡8)
3. “ነፍሴ በቅቤና በስብ እንደሚጠግቡ ትጠግባለች” (መዝሙር 63፡5)
ከላይ ያሉት ጥቅሶች ከመዝመረ ዳዊት ምዕራፍ 63 ላይ የተወሰዱ ሲሆን በከፊልም ቢሆን የጸሎትን ደረጃ ያሳያሉ ብዬ አስባለሁ፡፡ ጸሎት ወደ ውስጠኛው የእግዚአብሔር ማደሪያ የሚደረግ ግሥገሣ እንደ ሆነ ‹‹አምላኬ አምላኬ ወደ አንተ እገሠግሣለሁ›› (መዝ 63፡1) የሚለው ቃል ያመለክተናል፡፡ጉዞ መነሻ እንዳለው ሁሉ ጸሎታችንም ከውጨኛው የጸሎት አደባባይ ወደ ውስጠኛው የጸሎት አደባባይ ያነጣጠረ ነው፡፡ለዚህም ነው ዳዊት ‹‹ኃይልህንና ክብርህን አይ ዘንድ እንዲሁ በመቅደስህ ውስጥ ተመለከትሁ››(መዝ 63፡2) ብሎ የሚናገረው፡፡
ከላይ የጠቀስኩትን ክፍል ስናነብ የምንገነዘበው ነገር አለ፡፡እሱም ጸሎታችን እየጠለቀ በሄደ ቁጥር፣የእግዚአብሔርን ኃይልህንና ክብር የማየት በረከታችን እየጨመረ እንደሚሄድ ነው፡፡ለዚህ ነው በግልብ (superficial) ጸሎት‹‹ነፍሴ በቅቤና በስብ እንደሚጠግቡ ትጠግባለች›› (መዝ 63፡5) ማለት የማንችለው፡፡
‹‹እገሠግሣለሁ›› (ቁ.1) ስንልም የጸሎት ርምጃችን ጽናት፣ትግዕስት፣ንቁነት ወዘተ እንደ ግብዓት እንደሚያስፈልጉት መገንዘብ ይኖርብናል፡፡ብዙ ጊዜ ለጸሎት ስንደረደርና ለመገሥገሥ ስናስብ ‹‹ነፍሴ አንተን ተጠማች፤ሥጋዬ አንተን እንዴት ናፈቀች›› (መዝ 63፡1) የሚል መንፈስን ይዘን ነው የምንቀርበው፤በተጓዳኝ ተግዳሮቶቻችን እያሰብን፤ሕመማችን እያሰብን፤ፈተናዎቻችን እያሰብን፣መከራዎቻችን እያሰብን ወዘተ፡፡ባለፉት የጸሎት ጊዜያት የነበሩንን ግሩም ልምምዶች እያሰብንም አምላካችን አሁንም እንዲደግመው በመማጸን በፊቱ እንሆናለን፡፡
ጸሎትን ስንጀምር የመጸለይ ፍላጎታችን እጅግ ዝቅ ያለ ስለሚሆን፣ቶሎ እንድናቋርጥ ፈተናዎች ይመጣሉ፡፡ድካም ይጫጫነናል፤አእምሮአችን ይበታተናል ሌላም ሌላም፡፡ነገር ግን በጽናት ይህንን ተግዳሮት አሸንፈን ከዘለቅን፣የእግዚአብሔር ሕልውና የሚታወቀን ደረጃ ውስጥ እንገባለን፡፡በዚህ ደረጃ ላይ ሆነን ነው ‹‹ነፍሴ በኋላህ ተከታተለች››(መዝ 63፡8) የምንለው፡፡በዚህ ደረጃ ላይ ሆነን ነው‹‹ሳበን ካንተም በኋላ እንሮጣለን…..ከወይን ጠጅ ይልቅ ፍቅርህን እናስባለን››(መኃልይ 1፡4) የምንለው፡፡በዚህ ጊዜ ትንሽ ትንሽ ዝማሬና ምሥጋናም ያምረናል፤ጸሎታችንንም ሳናቋርጥ መቀጠል ያምረናል፡፡ቢሆንም ብዙ ሰዎች በሚገባ የጸለዩ ስለሚመስላቸው እዚህ ደረጃ ላይ ያቋርጣሉ፡፡እንዳውም ስለነበራቸው ድንቅ የጸሎት ጊዜም ለሰዎች ሊመሰክሩም ይችላሉ ብዬም አስባለሁ፡፡ይህንን ደረጃ ስናልፍ ሦስተኛው ደረጃ ውስጥ እንገባለን፡፡
ሦስተኛው የጸሎት ደረጃ፣ከጌታ ጋር እጅግ አስደናቂ ሕብረት የምናደርግበት የጸሎት ደረጃ ሲሆን፣እውነተኛ የሕይወት ለውጥ(transformation) ለማየት መልካም ዕድሎችን ይፈጥርልናል፡፡በዚህ የጸሎት ደረጃ አዘውትረን ስናሳልፍ ነው ‹‹ነፍሴ በቅቤና በስብ እንደሚጠግቡ ትጠግባለች፤ከንፈሮቼም ስምህን በደስታ ያመሰግናሉ››(መዝ 63፡5)ብለን በእውነት እና በድፍረት መናገር የምንችለው፡፡ይህ ደረጃ ‹‹መንፈስ ራሱ በማይነገር መቃተት የሚማልድበት››(ሮሜ 8፡27) የጸሎት ደረጃ ነው፤እንደ እግዚአብሔር ፈቃድም የምንጸልይበት፡፡እንባ ቋንቋችን ይሆናል፡፡ይሄ ደረጃ ሲጠልቅ፣ዝምታ ይበዛል፡፡እውነተኛ ንሥሓ ከአንደበታችን ይወጣል፡፡የከረምንበትን መንፈሳዊ ሕይወት በመንፈስ ስለምናየው ከልብ እናዝናለን፡፡ከጌታ ጋር ያለ ግብዝነት ለመራመድ የምንወስንበት ጊዜም ይሆናል፡፡ይህ ዓይነት ጸሎት በሕይወታችን ሲበዛ ነው፣መንፈሳዊ ለውጦችና ፍሬዎች የሚበዙት፡፡
ጌታ ሆይ እባክህ ወደ ጠለቀ ጸሎት ሳበን!
Wednesday, May 14, 2014
ከልብህ ሀዘንን አርቅ
ከልብህ ሀዘንን አርቅ
ወደ ስምንት አመት ገደማ ይሆናል፡፡በአንድ ከፍ ያለ የልብ ስብራት ውስጥ ሆኜ መቆዘም አብዝቼ ነበር፡፡ሐዘኔ ከበድ ያለ ስለነበር ከሰው ጋር መገናኘትና ማውራት አስጠልቶኝ ነበር፡፡በዛ ሁኔታ ውስጥ ሳለሁ የጌታ መንፈስ ደረሰልኝና አንድ ነገር አበራልኝ፡፡እርሱም ይህንን ያለሁበትን ሁኔታ የማራገፍ ሀላፊነት የኔ እንደ ሆነ በቃሉ ብርሃን ተገነዝብኩ፡፡የበራልኝ ቃል የሚገኘው መክብብ 11፡10 ላይ ያለ ቃል ሲሆን እንዲህ ይላል፡-
‹‹ከልብህ ሀዘንን አርቅ››
ይህ ቃል ልቤን ሰንጥቆ ነበርና የገባው ውስጤ በግርምት ነበር የተሞላው፤ለነበርሁበት ሁኔታም ‹‹የጊዜው ቃል›› ነበር፡፡አዝኜ የአጋንንት መጫወቻ ሆኜ እያላዘንሁ መቀመጥ እንደሌለብኝ በሚገባ ገባኝ፡፡ከዛም ከነበርሁበት ሁኔታ ለመውጣት ጌታ ጠንከር ያሉ ጸሎቶችን በመያዝ ትግል መጀመር እንዳለብኝ አመለከተኝ፡፡ባጋጣሚ የምኖርበት ቤት አጠገብ አንድ የመሠረተ ክርስቶስ አጥቢያ ቤ/ክ ነበርና እዚያ በፈረቃ ግቢውን የሚጠብቁትን ሰራተኞች እያስፈቀድሁ በጣም ረጅም ሰዓታት ባዶ አዳራሽ ውስጥ መጮህና መቃተት ጀመርሁ፡፡መጀመሪያ ይህንን ትግል ስጀምር ይሰማኝ የነበረው ስሜት ልክ ግምብ የመግፋት ያህል ነበር ፡፡የሚሰማኝ ስሜት ሳይበግረኝ በጸሎት መገሥገሥ ጀመርሁ፡፡በመሀል አንዳንዴ ካለሁበት ሁኔታ ጋር የሚሄዱ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችን እያጠናሁና እያሰላሰልሁ ከዚያ ደግሞ ቀጥዬ በመቃተትና የጌታ መንፈስ እንዲረዳኝ በመማጸን ሳልፈወስ ከምሽጌ ላልወጣ ለራሴ ቃል ገባሁ፡፡ለተወሰኑ ቀናት እንዲህ ባለ ሁኔታ ካሳለፍኩ በኋላ ሁኔታው ሁሉ ተገልብጦ ሰላምና ደስታ በማያቋርጥ ሁኔታ በልቤ ውስጥ ይፈስ ጀመር፡፡ዝማሬ፣ አምልኮ፣ስግደት ፣ውዳሴ ወዘተ በሕይወቴ ተትረፈረፈ፡፡ከዚያም ለረጅም ወራት እየጸለይኩ ውዬ ባድር ፤ስለጌታ ሳወራ ብውልና ሳመስግን ባድር ደስ ይለኝ እንደ ነበር ትዝ ይለኛል፡፡እዚህ ምድር ላይ ሁሉ የምኖር አልመስለኝ አለ፡፡የእግዚአብሔር ህልውና በሚገርም ሁኔታ እላዬ ላይ ነበር፡፡ብቻዬን ሆኜ ማንም ሳያወራኝ ሁሉ ሳቅ ያስፈነድቀኝ እንደነበር ሁሉ ትዝ ይለኛል፡፡መለኮታዊ ነበርና የነበርኩበትን ሁኔታ በቃላት መግለጽ ያዳግተኛል፡፡ክርስትና ዝም ብሎ ስርዓትና ወግ እንዳልሆነ ያስገነዘበኝም ክስተት ነበር፡፡ከጌታ ጋር በሚደረግ ሕብረት አስደናቂ በረከቶች ማፈስ እንደሚቻል ልቤ ላይ ትልቅ የሕይወት ማህተም አትሞልኝ የሄደ ድንቅ ጊዜ ነበርና ባሰብኩት ቁጥር ለጸሎት እነሣሣለሁ፡፡
ኢሳ 35፡10 ላይ የነበርኩበትን ሁኔታ የሚገልጸው ይመስለኛል፡፡እንዲህ ይነበባል፡-
‹‹እግዚአብሔርም የተቤዣቸው ይመለሳሉ እየዘመሩም ወደ ጽዮን ይመጣሉ የዘላለም ደስታ በራሳቸው ላይ ይሆናል ሀሴትንና ደስታን ያገኛሉ ሀዘንና ትካዜም ይሸሻሉ››
አዎ ያ ሁሉ ሐዘንና ትካዜ የት አንደገባ እስገሚገርመኝ ድረስ በሀሴት ተጥለቀለቅሁ፡፡ለዚህ ነው ኢሳ 10፡27 ‹‹በዚያም ቀን ሸክሙ ከጫንቃህ ቀንበሩም ከአንገትህ ይወርዳል ቀንበሩም ከውፍረት የተነሳ ይሰበራል››የሚለው፡፡ጠንከር ያሉና የጠለቁ ጸሎቶችን ስናበዛ የጌታ ጸጋ በውስጣችን እየጨመረ ስለሚሄድ ማንኛውንም አዚምና ሐዘን ለመስበር የምንችልበትን አቅምና ጉልበት እናገኛለን፡፡በጽኑነት ከልብ ሆነንና በቀጣይነት ሳንታክት በምንጸልየው ጸሎት ብዙ ድንቅ መለኮታዊ ነገሮችንም እናያለን ብዬ አምናለሁ፡፡ስለዚህ ከነካ ነካ የጸሎት ሕይወት ጌታ ወደ ጠለቀ ልምምድ እንዲከተን ሳንታክት ፊቱን ያለማቋረጥ እንሻ፡፡እንዲህ ብናደርግ ያስደንቀናል፡፡ስሙ ለዘላለም የተባረከ ይሁን!
Friday, May 9, 2014
ቀላይ ቀላይን ትጠራለች
May 9, 2014
ቀላይ
ቀላይን ትጠራለች/Deep calls deep (መዝ 42፡7)ረዘም ያለ ጸሎትን ስናስብ ምንም ብዙ ጊዜ በስጋ ብንጀምርም በመንፈስ እንደምንጨርስ ልናምን ይገባናል፡፡በጽኑነት እንደ ጌታ መንፈስ ምሪት ከቀጠልን በጸሎታችንም ድንቅ ነገሮችን እንደምናይ ምንም ጥርጥር የለኝም፡፡እዚህ ላይ ሊታሰብ የሚገባው ነገር፣ቶሎ እንድናቋርጥ እና ወደ ሌሎች ጉዳዮች እንድንሄድ ወደ ነፍሳችን ግብዣዎች ይመጣሉ፡፡ እነዚህን መንፈስን የማያረጋጉ መልእክቶች ወደ ጎን በማድረግና ጸሎታችን ላይ በሚገባ ትኩረት በማድረግ ብንገሠግሥ የጉትጐታው አስቸጋሪነት እየቀለለ መንፈሳችንና አእምሮአችን እየተወረሰ ወደ ድንቅ ሁኔታ ውስጥ እንገባለን፡፡“Start is always difficult” የሚባለውም እውነትነት ያለው ለዚህ ነው፡፡
ስለ ጸሎት ጥሩ ግንዛቤ ያላቸው ሰዎች ጸሎት ከሶስት በላይ እርከኖች (dimensions)እንዳሉት ይናገራሉ፡፡እንደዚህ ማሰቡም ብዙ ጊዜ ሲጠቅመኝ አይቻለሁ፡፡እነርሱም፡-
1.የውጨኛው አደባባይ(the outer court) ደረጃ
2.የመሀከለኛው አደባባይ(holy/the middle court) ደረጃ
3.የውስጠኛው አደባባይ/ቅድስተ ቅዱሳን(holy of holies) ደረጃ
ብዙዎቻችን በጸሎት ጊዜያችን የውጨኛውን አደባባይ ተሳልመንና የጌታን ጸጋ በሚገባ ሳንካፈልና በረከቱን ሳናይ ነው የምናቋርጠው ምንም እንኳ ዲሲፕሊን እንደሚያስፈልገን ብናምንም፡፡ለዚህ መፍትሔው በጽናት ወስኖ መቀጠል ነው፡፡አዘውትረንና ደጋግመን ስናደርገው ትግል መሆኑም ይቀራል፡፡እዚህ ደረጃ ላይ አእምሮአችን አስሩን ነገር ያስባል፣ይረግጣልም፡፡በዚህ ጊዜ የእንቅልፍ ስሜት፣ለመጸለይ ያለመነሣሣት እና ሌሎች ተቃራኒ ስሜቶች በሀይል ይታገሉናል፤የጠላት ከበባም ይኖራል፡፡
የመሀከለኛው አደባባይ የጸሎት ደረጃ የጌታ ህልውና የሚታወቀንና ለቀጣይ ጸሎት የምንነሣሣበት ደረጃ ነው፡፡“ሳበን ካንተም በኋላ እንሮጣለን” እያልን የጌታን ፊት በጨመረ ሁኔታ የምንፈልግበት የጸሎት ደረጃ ነው፡፡በዚህ ደረጃ ላይ የረካን መስሎንና በቂ ጸሎት የጸለይን
መስሎንና አንዳንዴም ተታለን ከጸሎት ልናቋርጥ አንችላለን፡፡እንደ መጀመሪያው ባይሆንም ጸሎታችንን የማቋረጥ ፈተናው እዚህም ደረጃ ላይ ቢሆን ከባድ ነው ማለቴ ነው፡፡ነገር
ግን ጨክነን በጽኑነት ከቀጠልን ወደ ሶስተኛው ደረጃ እንሻገራለን፡፡
የውስጠኛው አደባባይ የጸሎት
ደረጃ ብዙ ዝምታ የሚበዛበት፣በመንፈስ የምንቅታትበት፣እንባ ቋንቋችን የሚሆንበት፣ሮሜ
8፡26-27 ተግባራዊ የሚሆንበት፣ድንቅ ነገሮችን የምናይበትና በውስጣችን የሚታተምና የማይረሳ ክስተት የሚፈጠርበት የጸሎት ደረጃ
ነው፡፡እንደ እግዚአብሔር ፈቃድም በመንፈስ ስለምንጸልይ ጸሎታችን በሚገባ ይሰማል ብዬ አምናለሁ፡፡ይህ የጸሎት ደረጃ በህይወታችን
ሲበዛ እድገትና ለውጣችን በዛኑ ያህል ይጨምራል፡፡እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት የጸሎት ደረጃዎች ሉቃስ 11፡9 ላይ በግልጽ ሁኔታ ተቀምጠዋል፡፡እነርሱም ፡-
1.የመጠየቅ ደረጃ(the asking realm)፡-የመጀመሪያው የጸሎት ደረጃ ሲሆን፣በአእምሮአችንና በሥጋ የምንጸልየው ጸሎት ነው፡፡ማለትም እንዲሆኑልን የምንፈልጋቸውን ጉዳዮች በአአምሮአችን የምናሳውቅበት የጸሎት ደረጃ ነው፡፡
2.የመፈለግ ደረጃ(the seeking realm)፡-የጌታን ፊት በሀይል የምንፈልግበት የጸሎት ደረጃ ሲሆን፣ጠንከር ያለ ፀሎት የምንጸልይበትና የጌታ መንፈስ እስኪሰማን ድረስ የምንጸልየው ጸሎት ነው፡፡
3.የማንኳኳት ደረጃ(the knocking realm)፡-ይህ ጸሎት ቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ ለመግባት የምንጸልየው ጸሎት ነው፡፡ይህ የጸሎት ደረጃ ትግዕስት ያለበት፣የመንፈስ ቅዱስን ምሪት በንቃት መከታተል ያለበት፣ምስጋና ያለበት፣ንስሀ እና እንባ መገለጫዎቹ የሆኑበት የጸሎት ደረጃ ነው፡፡ከዚያም አንዴ ቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ ከገባን በኋላ ቃላት ውሱን ይሆናሉ፤ ዝምታ ይበዛል፡፡በዚህ ጊዜ በትክክል በመንፈስ እንጸልያለን፡፡በማይነገር መቃተት እንደ ጌታ ፈቃድ የምንጸልበትና የምንማልድበት ጊዜም ይሆናል፡፡
ግሩም የሆነ የጸሎት ሕይወት እንዲኖረን የሚያደርገን ውሳኔ ነው፡፡ከቤት ማልደን ተነስትን ሳናረፍድ መሥሪያ ቤታችን የምንሄደው በውሳኔ ነው፤አዘውተረን ስላደረግነው ተነስተን ለመሄድ ምንም አንቸገርም፡፡ያንን መርህ ጸሎታችን ላይ በተግባር ማዋል አለብን፡፡እኔ ቢሰማኝም ባይሰማኝም አልነሳም ከጸሎት ብዬ የምወስንባቸው ብዙ ጊዜዎች አሉ፡፡እንዳውም እንዳልጸልይ በከበደኝ ጊዜ ገፍቼ ብዙ ሰዓት በውሳኔ ስጸልይ ካሰብሁት በላይ አስደናቂ ጊዜን አሳልፌ አውቃለሁ፡፡ባብዛኛው በራሴ ህይወት እንደማየው ጸሎታችንን እንድናቋርጥ ወደ አእምሮአችን የማይመጣ የፈተና አይነት የለም ነገር ግን ተቁነጥንጠን ስንነሳ ያንኑ የምናውቀውን ሕይወትና ኑሮ ነው የምንቀጥለው፡፡ ከጌታ ጋር ብናሳልፍ ግን ሕይወታችን እየተለወጠና የጌታ ጸጋ በሕይወታችን እያደገ ይመጣል፡፡አለበለዚያ ግን ልንመኝ ልናስመስል እና ዝም ብሎ በባዶው ልንጓጓ እንችል ይሆናል እንጂ በነካ ነካ ጸሎት የእግዚአብሔርን ክብርና ጉብኝት አናይም፡፡ ስለዚህ መልካሚቱ እጁ በመካከላችን እንድትበዛ በጸሎት እንጋደል!
ጸሎት ፡-ጌታ ሆይ ከዳር ዳር ጸሎት እባክህ ክብርህን ወደምናይበት የጸሎት ጥልቀት ውስጥ ክተተን!
በቀለ በላቸው(ዶ/ር)
240-330-5004
Subscribe to:
Posts (Atom)