Friday, November 29, 2013

የመከራ እሳት እና መፍትሄው



የመከራ እሳት እና መፍትሄው

ወደ ህይወታችን የማይመጣ የፈተናና የመከራ አይነት የለም፡፡መጽሀፍ ቅዱስን ስናጠና አብዛኛዎቹ የእግዚአብሔር ሰዎች በብዙ ፈተናና መከራ ውስጥ እንዳለፉ እናስተውላለን፡፡እያንዳንዱን ፈተና በእግዚአብሔር ጸጋ እና ምሪት ተደግፈን እና ኢየሱስን እያየን ከተጋፈጥነው እምነታችን እየጠነከረና ወደ ፊት ተመሳሳይ ነገሮች ሲገጥሙን የምንመክትበትን አቅምና ጥበብ እየጨመርን እንመጣለን፡፡


በአዲስ ኪዳን መጻህፍት ውስጥ ሃዋርያው ጳውሎስ ስለ ወንጌል እጅግ ከፍ ያሉ መስዋእቶችን እንደከፈለ በጽሁፎቹ ውስጥ እናስተውላለን፡፡እነዚህንም መከራዎች በእግዚአብሔር ጸጋ ተቋቁሟቸውም እንዳለፈ ጽፎልናል፡፡2 ቆሮ 4፡7-10 በውስጣችን እግዚአብሔር ካስቀመጠው መዝገብ የተነሳ የሚደርሱብንን መከራዎች ዘርዘሮ አስቀምጧቸዋል፡፡እነርሱም እንዲህ ይነበባሉ፡-

  • እንገፋለን

  • እናመነታለን

  • እንሰደዳለን

  • እንወድቃለን

  • የኢየሱስን ሞት በስጋችን ተሸክመን እንዞራለን

  • ዘወትር ለሞት አልፈን እንሰጣለን

ክርስትያን ከመሆናችን የተነሳ ብዙ ነገሮች ይደርሱብናል፡፡የመከራው እና የፈተናው መጠን እንደ እንቅስቃሴያችን መጠን ይወሰናል፡፡ብዙ ለወንጌል የምንሮጥ ከሆነ የተግዳሮቱና የስቃዩ ብዛት እንደዛው ያይላል፡፡ጌታን ለማገልገል ደፋ ቀና በምንል ክርስትያኖች ላይ ሰልፉ እጅግ ብርቱ ነው፡፡ጠላት በተለያየ መንገድ ተስፋ ለማስቆረጥ እና ሩጫችንን እንድናቆም የማይልከውና የማያመጣው ተግዳሮት የለም፡፡


የሃዋርያው ጳውሎስን ጽናት እንድንገረም የሚያደርገን ቃል 2 ቆሮ 4፡16-17 ላይ እናገኛለን፡፡እንዲህ ይላል፡-‹‹…አንታክትም ነገር ግን የውጭው ሰውነታችን ቢጠፋ እንኳ የውስጡ ሰውነታችን እለት እለት ይታደሳል››በዚህ ቃል ላይ ሀዋርያው ጳውሎስ ለውጫዊው ማንኛውም ነገር ደንታ እንዳልነበረው እናያለን፡፡ይልቁንም ውስጣዊ ማንነታችን ላይ ትኩረት ማድረግ እንዳለብን ያስገነዝበናል፡፡ምክንያቱም ማንኛውም ውጫዊ ነገር ጠፊ ነውና ነው፡፡‹‹የውጭው ሰውነታችን ቢጠፋ››የሚለው ሀረግ የሰውነታችንን መጎሳቆል ብቻ የሚወክል ብቻ ሳይሆን ማንኛውንም የምናጣቸውንና የሚጎድሉብንን ማንኛውንም ውጫዊ ነገሮችን ሁሉ ይወክላል፡፡በተለያዩ ጫናዎች ውስጥ ስናልፍ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በቂ ህብረት እያደረግን ከተጣበቅን የውስጡ ሰውነታችን እየታደሰና እየጠነከረ ስለሚሄድ የጠለቀ ህብረት ውስጥ እራሳችንን እናገኘዋለን፤ጌታንም ልዩ በሆነ መንገድ እያወቅነው እንመጣለን፡፡እዚህ ዘላለማዊ ትርፍ ላይ ነው ትኩረትም ማድረግ ያለብን፡፡


ሮሜ 5፡3-5 ላይ ያለው ቃል የመከራን መለኮታዊ ጥቅም እንዲህ ባለ ተዋረድ ያስቀምጠዋል፡-
ፈተና-------›ጽናት----------›መገለጫ ባህርይ---------›ተስፋ
በምናልፋቸው መከራዎች የጌታ የማዳን ክንድ እና አብሮነቱ እየታወቀንና እምነታችን እና ተስፋችን እየጨመረ ይሄዳል፡፡ተስፋ የምናደርገው ዘላለማዊ ህይወት ደግሞ ማስረጃ እና የሚጨበጥ ነገር በሚገባ አለው፡፡ተስፋው በፍጹም የሚያሳፍር አይደለም ለምን ቢባል ለተስፋው ማረጋገጫ የሚሆን የመንፈስ ቅዱስ ፍቅር በሚገባን እና በሚታወቀን መልኩ በልባችን ስለፈሰሰ ነው፡፡


ወደ ህይወታችን የሚመጣው ፈተናና ተግዳሮት ያለንን እምነትና ጽኑነት በሚገባ ይፈትሸዋል፡፡ወርቅ በእሳት እንደሚነጥር እና እላዩ ላይ ያሉት የማይረቡ ነገሮች እንደሚወገዱ ሁሉ የሚመጣው የመከራ እሳት አላስፈላጊ ነገሮችን እየጣል ከጌታ ጋር የበለጠ እንድንጣበቅ ያደርገናል፡፡ከዚህ የተነሳ ለጌታ ያለን ምስጋናና አምልኮ ልዩ ነው የሚሆነው-የማዳን እና የማጽናናት ክንዱን በሚገባ እንቀምሳለንና!ይህንን ሀሳብ በሚገባ የሚገልጽ ቃል 1ጴጥ 1፡6-7 ላይ እናገኛለን፡፡እንዲህ ይነበባል፡፥‹‹በእሳት ምንም ቢፈተን ከሚጠፋው ወርቅ ይልቅ አብልጦ የሚከብር የተፈተነ እምነታችሁ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ ለምስጋናና ለክብር ለውዳሴም ይገኝ ዘንድ አሁን ለጥቂት ጊዜ ቢያስፈልግ በልዩ ልዩ ፈተና አዝናችኋል››እጅግ የሚገርም ቃል ነው፡፡ፈተናው እምነታችን እንዲጠነክር እና ከጌታ ጋር እንድንጣበቅ ትልቅ አጋጣሚን ፈጥሮልን ያልፋል፡፡ስለዚህ ያለው መለኮታዊ ትርፍ ቀላል አይደለም፡፡ስለዚህ ፈተናን በዚህ እይታ(perspective) ነው መመልከት ያለብን፡፡ፈተናው ለጊዜው ያሳዝነናል፣ልባችን ይሰበራል እንዳውም የማንነሳ እስኪመስለን ተስፋ ልንቆርጥ እንችላለን ነገር ግን መከራው ለህይወታችን አስፈላጊ የህይወት ቅመሞችን ሰጥቶን ያልፋል፡፡


በእራሴ ህይወት አንገት የሚያስደፉ ብዙ ችግሮች ደጋግመው ደርሰውብኛል፡፡በእነዚያ ጊዜዎች እንደ ሰው በሀይል አዝኛለሁ፡፡ተስፋ እስከ መቁረጥ የደረስኩባቸውም ጊዜዎችም ነበሩ፡፡ወደ ልቤ ተመልሼ እርሱ የመፍትሄ አምላክ መሆኑን እና ከእነዚያ ጉዶች ሊያወጣኝ እንደሚችል በመረዳቴና እራሴን በጸጋው ዙፋን ፊት በመጣሌ እና ችግሩ እስኪያልፍ በጸሎት መንፈስ ውስጥ በመሆኔ የሚገርመውን የማጽናናት ክንዱን፣ቸርነቱንና ምህረቱን በሚገባ አይቻለሁ፡፡እርሱን ማን ይመስለዋል?እንደርሱስ አጽናንቶና ህይወትን አድሶ እንደገና የሚያቆም ማን አለ?


አዎ በእርግጠኝነት መከራው ያልፋል፡፡በዚህ ጊዜ ውስጥ ምን እናድርግ የሚለው ነው ትልቅ ዋጋ ሊሰጠው የሚገባ ቁም ነገር ነው፡፡በዚህ ጊዜ የመጽናናት አምላክ እንደ ሀሳቡ ከነገሩ ውስጥ እስኪያወጣን ድረስ ሙሉ በሙሉ የጸሎት ክተት ማወጅ አለብን ብዬ አምናለሁ፡፡እኔም የማደርገው እንደዚያ ነው፡፡በዚህ ጊዜ ጠንከር ያሉ ጸሎቶችን ለረጅም ሰአታት መጸለይ እጅግ ይጠቅመናል፡፡ለምን ቢባል በስጋችን እና በነፍስ ትግል ፈተናውን መቋቋም ስለማንችል ነው፡፡ለእኛ የሚያስፈልገን የእግዚአብሔር ጸጋ ነው፡፡የእግዚአብሔር ጸጋ ደግሞ በችግር ውስጥ ተከበንም ቢሆን  ቅንጣት ሳይሰማን ደግፎ ሊያቆመን ይችላል፡፡ክርስትናን ልዩ የሚያደርገውም የእግዚአብሔር ጸጋ ነው፡፡ለዚህ ነው ማቴ 11፡28 ‹‹እናንተ ሸክማችሁ የከበደ ወደ እኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለሁ›› የሚለው፡፡እዚህ ቃል ውስጥ ያለው በረከት ታላቅ ነው፡፡በትንሹም ቢሆን ቀምሸዋለሁና እጅግ ደጋግሜ የማነሳውና የምወደው ቃል ነው፡፡አዎ ማሳረፍ ብቻ ሳይሆን ይገላግል፡፡ስለዚህ በእራስ ከመታገል እና ሰዋዊ መፍትሔዎችን በመዘየድ የእረፍት ዘመናችንን ከማርዘም በልዑሉ መጠጊያ ውስጥ መጥተን እንረፍ፤ሁለንተናችንንም ለእርሱ እንስጥ!


No comments:

Post a Comment