Friday, November 8, 2013

በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ



በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ

ይህ ጽሁፍ ዮሀ 15፡1-11 ላይ የሚያተኩር ሲሆን ኢየሱስ በዚህ ምእራፍ ላይ ሊገባን በሚችል ምሳሌያዊ ቋንቋ በመጠቀም ከእርሱ ጋር የምናደርገው የጠበቀ ህብረት እና ግንኙነት በክርስትና ህይወታችን ወሳኝ እንደሆነ ያሳየናል፡፡ዮሀ 15፡4 ላይ ‹‹በእኔ ብትኖሩ እኔም በእናንተ››የሚል ድንቅ መርህ እናገኛለን፡፡አያይዞም እዛው ቁጥር 4 ላይ ‹‹ቅርንጫፍ በወይኑ ግንድ ባይኖር ከራሱ ፍሬ ሊያፈራ እንዳይቻለው እናንተ ደግሞ በእኔ ባትኖሩ አትችሉም››በማለት ከእርሱ ጋር ያለን ህብረት እና ግንኙነት ለፍሬ ማፍራታችንም ወሳኝ እንደሆነም ያስገነዝበናል፡፡አዎ በህይወታችን ትልቅ ቦታ ሊይዝና እንቅስቃሴዎቻችንን ሁሉ ሊቆጣጠር የሚገባው ‹‹በእኔ ብትኖሩ እኔም በእናንተ›› የሚለው የፍቅር መርህ ነው፡፡ቁጥር 7 ላይ እንደገና አስረግጦ እንዲህ ይላል፡-‹‹በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ ይሆንላችሁማል››ስለዚህ አንድ የማያሻማን ነገር የስኬታችን ቁልፍ ሚስጥር ያለው በእርሱ ህልውና ውስጥ መኖራችን ሲሆን የሚጨበጥ ፍሬ ያለው ክርስትና ለመኖር የሚከተሉት ሁለት የፍቅር መርሆዎች በሚገባ መተግበር አለባቸው፡-

  • በእርሱ መኖር

  • ቃሎቹ በእኛ ውስጥ መኖር

‹‹በእኔ ብትኖሩ››የሚለው ሀሳብ በዳግመኛ ልደት መንፈስ ከሆነው ቃል በመወለድ ይጀምራል፡፡ይህ አስደናቂ መንፈሳዊ ለውጥ በውስጣችን ከተከናወነ በኋላ ህልውናው ውስጥ እንድንኖር የሚያደርገን ከቃሉ ጋር የምናደርገው ህብረት እና ቀጣይነት ያለው ጸሎት ነው፡፡በትጋት እየጸለይን በፊቱ በቂ ጊዜን ስናሳልፍ እያወቅነውና ከእርሱ ጋር እየተጣበቅን እና ጸጋው በሕይወታችን እየበዛልን ይመጣል፡፡ከዚህም የተነሳ ከአለም እየተለየንና መንፈሱን ከሚያሳዝኑ ነገሮች እየራቅን ስለምንመጣ ህልውናው በሚገባ እየታወቀን እና አብሮነቱን እየተሰማን መዋል ማደር እንጀምራለን፡፡ይህ በረከት ወደ እኛ እንዲመጣ የሰው ሀላፊነት መኖሩ ምንም አያጠያይቅም፡፡ማለትም አዘውትረን በጸጋው ዙፋን ስር መውደቅና ፊቱን መፈለግ ይኖርብናል፡፡


‹‹ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ››የሚለውን ሀሳብ እንደዚህ ማስቀመጥ ይቻላል፡፡በተለያየ መንገድ ማለትም በስብከት፣መጽሀፍ ቅዱስን በማጥናትና የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸውን መጽሀፍት በማንበብ ወደ ውስጣችን የሚገቡት የእግዚአብሔር ቃሎች መጀመሪያ በአእምሮአችን በኩል ነው ወደ መንፈሳችን ወይም ወደ ውስጥ ማንነታችን የሚገቡት፡፡በአእምሮአችን የተቀበልነው ቃል ወደ ውስጥ ማለትም ወደ መንፈሳችን የሚወርደውም ቃሉን ስንረዳውና ስናስተውለው ነው፡፡ያስተዋልነውና የተረዳነው በብዙ ትጋት ከውስጣችን ጋር ያዋሀድነው ቃል ነው ውስጣችን ሊቆይና ሊኖር  የሚችለው እንደዚህ እንደሚል፡-‹‹በማያስተውል ላይ ሌባው ይመጣል››፡፡ ያስተዋልነውን ቃል ሌባው በፍጹም ሊነጥቀን አይችልም፡፡ስለዚህ እዚህ ጋ ጥሩ ዋጋ መክፈል ይኖርብናል፡፡እብራውያን ምእራፍ ሶስት ላይም ‹‹የሰሙት ቃል ከሰሚዎቹ ጋር በእምነት ስላልተዋሀደ አልጠቀማቸውም››የሚል ገራሚ ሀሳብ እናገኛለን፡፡አእምሮአችን ውስጥ የሚዘሩት ቃሎች ወደ ውስጣችን ዘልቀው እንዲዋሀዱ ብዙ ማሰላሰል፤ብዙ ጥናት እና በህይወታችንም በተግባር መፈጸም ይገባናል፡፡እንዲህ ስናደርግ ነው ቃሉ በእኛ ውስጥ የሚኖረው፡፡በተለይ ያነበብነውን ቃል በተግባር ማዋል ውስጣችን በማይረሳ መልኩ እንዲታተም ስለሚያደርገው በልባችን ላይ በማይፋቅ መልኩ ይጻፋል፡፡


ቁጥር 5 ላይ እንደገና አስረግጦ ያለ እርሱ ምንም አይነት እመርታ እና ስኬት እንነደማይኖረን እንዲህ በማለት ይነግረናል፡-‹‹ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ እርሱ ብዙ ፍሬ ያፈራል››፡፡‹‹ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉም›› የሚለው በህይወታችን ሬማ ካልሆነ እና ካልበራልን ያለ እርሱ ብዙ ልንኳትን እንችላለን፡፡እግዚአብሔር በህይወቴ ይህንን ቃል በሚገባ እስካየውና እስክታዘዘው ድረስ ጉልበቴን ገንዘቤን እና ጊዜዬን ጨርሻለሁ፡፡አሁን ጌታ ይመስገን ጌታ በጥሩ ሁኔታ መልሶኛልና ያለ እርሱ ምንም ማድረግ እንደማልችል ገብቶኛል፡፡በእንቅስቃሴዎቼ ሁሉ እርሱን ለማስቀደም ወስኛለሁ፡፡
በነገራችን ላይ በእነዚህ በላይ በተጠቀሱት የቃል መርሆዎች ህይወታችን ሲለካ ያለነው እታች እንደሆነ በመንፈሴ አስተውላለሁ፡፡ለምን ቢባል፡-

  • በቂ የሆነ የጸሎት ህብረት የለንም

  • ቃሉን በቂ ጊዜ ሰጥተን አናነብም አናጠናውም አናሰላስለውም(ጊዜያችንን የሚቀሙ ብዙ ነገሮች አሉ)

  • ቃሉን በተግባር ደረጃ አንለማመደውም

ከዚህ የተነሳ በአካባቢያችንና በህብረተሰባችን ላይ ተጽእኖ የሚያመጣ ፍሬ አይታይብንም፡፡የሰማዩ አባታችን በህይወታችን እንዲከብር እና በእኛ ህይወት እርሱን እንዲያዩና ወደ እርሱ ዘወር እንዲሉ ካስፈለገ ከላይ ወደ ተጠቀሱት ትእዛዞችና መርሆዎች በሚገባ መመለስ ይናርብናል፡፡አለበለዚያ ዝም ብለን ልናስመስል እንችል ይሆናል እንጂ እነዚህን መሰረታዊ የሆኑ ነገሮችን ሳንተገብር በፍጹም ፍሬ የሚባል ነገር እንደማይኖረን ልናውቅ ይገባል፡፡

ስለዚህ ሁለቱ ከላይ የተጠቀሱት ሁኔታዎች ሲሟሉ (በእርሱ ስንኖር እና ቃሎቹ በእኛ ውስጥ ሲኖሩ) ፡-

  • አንድ ክርስትያን ከግንዱ ጋር ተጣበቀ ማለት ይቻላል

  • እውነተኛ ፍሬም የማፍራት ችሎታ ይኖረዋል

ይህንን ፍሬ በሶስት ከፍለን ልናየው እንችላለን ምንም እንኳ አንድ የሚያመሳስል ግብ ቢኖራቸውም (ክርስቶስን ማሳየት)

  • የመንፈስ ፍሬዎች (ገላ 5፡22 እንደሚል፡-‹‹የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፥ የውሃት፥ ራስን መግዛት ነው››)

  • በበጎ ስራ የምናፈራቸው ፍሬዎች(ቆላ 1፡10-11 እንደሚል ‹‹በበጎ ሥራ ሁሉ ፍሬ እያፈራችሁ››)-ማህበራዊ የሆኑ ስራዎችን ይወክላል

  • የወንጌል ስራ ፍሬዎች


ወረድ ብሎም ‹‹በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ ››የሚለውን የፍቅር ትእዛዝ ስንተገብር ስለሚገጥመን በረከት እንዲህ በማለት ይገልጻል፡-
1.የምትወዱትን ለምኑ ይሆንላችኋል(ቁጥር 7 ላይ)
2.ደስታችሁም ሙሉ ይሆናል(ቁጥር 11 ላይ)

እነዚህን ሁለት በረከቶች ሳስብ ይገርመኛል፡፡ምን አይነት መታደል ነው፤የሚደንቅ ህይወት!!ወደ እንደዚህ አይነት መንፈሳዊ ህይወትና ልምምድ ውስጥ እግዚአብሔር ሊከተን ይፈልጋል ግን እንደሚገባኝ መጀመሪያ ግን ለእርሱ በሚገባ መገኘት ያስፈልገናል ብዬ አምናለሁ፡፡ስለዚህ ይህንን  መንፈሳዊ በረከት በሕይወታችን ለማየት ሳንታክት በትጋት ፊቱን እንፈልግ !!!



No comments:

Post a Comment