Friday, August 28, 2015

ልባሞች የሆናችሁ አይምሰላችሁ (ሮሜ 12፡16)

ይህን ቃል ጊዜ ሰጥታችሁ አስባችሁትና አሰላስላችሁት ታውቃላችሁ ? በዚህ ሳምንት ለእኔ የሚገርም ቃል ሆኖ ነው የከረመው፡፡እስቲ አስቡት፡፡አንዳንዴ ግሩም ስብከት ወይም ትምህርት ታስተምሩና፣አድናቆት የተቸረው ሥራ ታከናውኑና፣ስኬት የተጐናጸፈ ክንውን ትፈጽሙና፣ራሳችሁ ለራሳችሁ ፣ “እኔ ኮ ማን ይችለኛል፣ጎበዝ እኮ ነኝ ፤ማን ይበልጠኛል ?” ብላችሁ አታውቁም ?

በግሌ ልቤ የታበየበትና እራሴን ያሞካሸሁበት ብዙ ጊዜያት እንደ ነበሩ አልደብቃችሁም፡፡ብዙዎቻችን ጌታ ማስተዋል ካልሰጠን ለጌታ ልንሰጥ የሚገባውን ምሥጋናና ክብር ሊያሳንስ የሚችል አላዋቂነት አይጠፋንም ብዬ አስባለሁ፡፡ከዚህ ስህተት ጌታ ይጠብቀን! የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ብሎ አስረግጦ ይናገራልና፡-“ያልተቀበልኸው ምን አለህ ? የተቀበልህ ከሆነ ግን እንዳልተቀበልህ የምትመካ ስለ ምንድን ነው ?” (1 ቆሮንቶስ 4፡7)

ወገኖቼ እስቲ ደጋግማችሁ አስቡት፡፡እስቲ ምንድን ነው ያልተቀበልነው? የራሳችን የምንለው ነገር የቱ ነው ? መጠቀሚያ ዕቃዎች ነንና! በቃ ይኸው ነን፡፡ስለዚህ እጅግ ልናስተውል ይገባል፡፡የእግዚአብሔር ቃል “እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማል፤ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል” (ያዕቆብ 4፡6) ይላልና ሁልጊዜ አመለካከታችን በትሕትና መቃኘት ይኖርበታል ብዬ አምናለሁ፡፡ምክንያቱም እግዚአብሔር በምሕረቱና በረድኤቱ በሚታመኑ ነውና ደስ የሚሰኘው፤የሚደገፉበትን ይረዳል፣ይደግፋልም፡፡

በራሳችን፣በዕውቀታችንና በማናቸውም ምድራዊ ነገሮች መደገፍና ትምክህት አይጠቅመንም፣ይጐዳናል እንጂ፡፡የሚመካ ሰው ለሚታመኑበት አስተማማኝ በሆነው የፍቅር አምላክ ነው ሊመካ የሚገባው፡፡ቃሉ እንዲህ ብሎናልና፡-

“ጠቢብ በጥበቡ አይመካ፣ኃያልም በኃይሉ አይመካ፣ባለ ጠጋም በብልጥግናው አይመካ፤ነገር ግን የሚመካው። ምሕረትንና ፍርድን ጽድቅንም በምድር ላይ የማደርግ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን በማወቁና በማስተዋሉ በዚህ ይመካ፤ ደስ የሚያሰኙኝ እነዚህ ናቸውና፣ይላል እግዚአብሔር” (ኤርምያስ 9፡23-24)

ደግሜ እላለሁ፣ልባሞች የሆንን አይምሰለን፡፡ያለ እሱ ፈቃድ፣ድጋፍና ረድኤት፣ከፊታችን ተዘጋጅቶ የቀረበውን እንጀራ ቆርሶ ወደ አፍ ማድረግ እንኳ ከባድ ነው፡፡ስለዚህ ሁሌም በትሕትናና በምስጋና መንፈስ በፊቱ እንሁን፡፡የተደረገልን ነገሮች በመንፈስ እያየን እናክብረው፣ከፍ እናድርገው፡፡ተባረክ እንበለው፤በዚህ ደስ ይሰኛልና!

Sunday, August 23, 2015

Notice

 
To all my followers.I am living in Gaithersburg,Maryland.I wrote three books in Amharic.The first one is my autobiography,the second one is a collection of 75 poems and the third one is on The Benefits of Prayer.The books are very cheap and affordable.So,you can contact me with the following ways.
My phone :2403305004
My email :beke_abay@yahoo.com
I can be contacted thru facebook
Be blessed

Wednesday, August 19, 2015

yegizewkal.org

የእግዚአብሔርን እንጂ የሰው አናስብ


በማቴዎስ ምዕራፍ 16፣ጌታችን ኢየሱስ “ብዙ መከራ ይቀበል…..እንዲገባው” (ቁ.11) ለደቀ መዛሙርቱ በነገራቸው ጊዜ፣ጴጥሮስ ወደ ነበረበት ጠጋ ብሎ “አይሁንብህ ጌታ ሆይ ይህ አይደርስብህም”(ቁ.22) ብሎት ነበር፡፡ጌታ ኢየሱስም ወዲያው “ወደ ኋላዬ ሂድ አንተ ሰይጣን የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብምና ዕንቅፋት ሆነህብኛል” (ቁ.23)ብሎ ገሥጾታል፡፡

አዎ፣ጴጥሮስ በዛ ጊዜ የእግዚአብሔርን አልነበረም ያሰበውና ያደረገው፡፡ቢሆንም ከኢየሱስ ትንሣኤ በኋላና ታላቁን ተልዕኮ ተቀብለው ከተሰማሩ በኋላ፣ብዙ መከራን ተቀብሎ ያለፈ ትልቅ ሐዋርያና የእምነት ጀግና እንደ ነበር ታሪክና መጽሐፍ ቅዱስ ዘክረውታል፡፡ይህ ሐዋርያ የክርስቶስን መከራ በመካፈል ዙሪያ ጠንካራ መልእክቶችን መጻፉም ይታወቃል፡፡ከነዚህ መልእክቶቹ በሁለት ክፍሎች ላይ እንዲህ ብሏል፡-

“ወዳጆች ሆይ በእናንተ መካከል እንደ እሳት ሊፈትናችሁ ስለሚሆነው መከራ ድንቅ ነገር እንደ መጣባችሁ አትደነቁ፤ነገር ግን ክብሩ ሲገለጽ ደግሞ ሐሤት እያደረጋችሁ ደስ እንዲላችሁ በክርስቶስ መከራ በምትካፈሉበት ልክ ደስ ይበላችሁ”(1የጴጥሮስ 4፡12-13)

“በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዘላለም ክብሩ የጠራችሁ የጸጋ ሁሉ አምላክ ለጥቂት ጊዜ መከራ ከተቀበላችሁ በኋላ ፍጸማን ያደርጋችኋል፣ያጸናችኋል፣ያበረታችኋል”(1ጴጥሮስ 5፡10)

ልብ በሉ፤እነዚህን ጠንካራ መልእክቶች “አይሁንብህና አይድረስብህ” ያለው ጴጥሮስ ነው የጻፋቸው፡፡አይገርምም! በበኩሌ ሁሌ እነዚህን መልእክቶች ባነበብኩና ባሰላሰልኩኝ ቁጥር ይህንን ሰው ያገኘው ለውጥ ይደንቀኛል፡፡እንዲህ ሊል የቻለበት ምን ዓይነት ጥልቅ መንፈሳዊ ለውጥና መረዳት እንዳገኘው ገና በሚገባ ጥርት ብሎ አልገባኝም፡፡ነገር ግን ከጌታው ጋር የነበረው እጅግ የተጣበቀ ሕይወት ይኼንን ድፍረትና ትምክህት እንዳመጣለት አልጠራጠርም፡፡

ጌታ ኢየሱስ ጴጥሮስን ከገሠጸው በኋላ አስተሳሰባቸውንና አመለካከታቸውን ለማስተካከል ይመስላል፣ወዲያውኑ የክርስትያኖች ዋና ማገር የሆነውነንና ዘመን የማይሽረውን መልእክት የሰጣቸው፡፡መልእክቱ እንዲህ የሚል ነው፡-

“እኔን መከተል የሚወደ ቢኖር ራሱን ይካድ፤መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ፡፡ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ሁሉ ያጠፋታል፤ስለ እኔ ግን ነፍሱን የሚያጠፋ ሁሉ ያገኛታል”(ማቴዎስ 16፡22)

በዚህ ዘመን በዚህ ቃል ዙሪያ ብዙ ስብከትና ትምህርት እምብዛም አይሰማም፡፡ዛሬ ላይ የምንገኝ አማኞች(ብዙዎቻችን) በግብራችን እንደ ጴጥሮስ(ከመለወጡ በፊት) ዓይነት አመለካከትና አስተሳሰብ ያለን ይመስለኛል-“አይሁንብህና አይድረስብህ” የምንል፤የመስቀሉን መንገድ የምንሸሽ!
በፍጹም ዋጋ የሚያስከፍሉ፣ሕመም ያለባቸውንና መከራን የሚያመጡ ነገር ግን ክርስቶስ የሚከብርባቸውን ነገሮች አቋራጭ እየፈለግን እየሸሸንና እያመለጥን ያለን ይመስለኛል፡፡

ብዙዎቻችን በራስ ወዳድነት፣በስስትና በራስ ተኮር የኑሮ ዘይቤ ተጠላልፈን እራሳችኑኑ ስናስብና ስንከባከብ ነው ውለን የምናድረው(ምናልባት ተሳስቼ ከሆነ ልታረም እችላለሁ)፡፡የሕይወት ዘይቤአችን ይህንን ያለ ምንም ችግር የሚያሳብቅም ይመስለኛል፡፡እውነተኛና የምር የሆነ የክርስትና ሕይወትና ሩጫ ግን ይህንን አካሄድ በፍጹም አያስተምርም፣አያደፋፍርም፡፡ሕይወቱ በሚገባ ይተግበር ከተባለ “ለሌሎች የመኖርና ለሌሎች የመቆረስ ሕይወት”፣እንዲሁም "የመስቀል መንገድ" መሆኑ ሊታወቅና ሊሰመርበት ይገባዋል፡፡

በነገራችን ላይ ይህ ጽሑፍ ሰዎችን ለመውቀስ ታስቦ ሳይሆን፣በዚህ ዙሪያ ያለንን አመለካከትና አስተሳሰብ እንድናርቅ ሊረዳን ይችላል ብሎ ከማሰብ የመነጨ እንደ ሆነ እንዲታሰብልኝ እፈልጋለሁ፡፡

ሕይወት በምርጫዎችና በፈተናዎች የተሞላች ናትና በመንገዳችን ላይ ኢየሱስ የሚከብርባቸው ለጊዜው ግን የሚያሳምሙን ብዙ ጉዳዮች ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ለምሳሌ በእነዚህ የፈጠራ ምሳሌዎቼ ላይ ብትገኙ ምን ታደርጋላችሁ?

• ሰው ታሞ በመኪናችሁ እንድታደርሱት ቢጠይቃችሁና የተጠራችሁበትና የማትቀሩበት ሠርግ ቢኖር
• በእጃችሁ ያላችሁ 200 ብር ብቻ ነው፡፡ነገር ግን ያንን 200 ብር እጅግ በጣም ለአንገብጋቢ የሕይወት ጉዳይ የሚፈልግ ወንድም አጠገባችሁ ቢኖር
• እጅግ ግሩም የሆነ ሰው ሁሉ ተጠራርቶ እየሄደበት ያለበት ኮንፈረስ ላይ ለመሄድ እያሰባችሁ፣የታመመና የእናንተ ጉብኝት የሚያስፈልገው ወንድም ቢኖር

እናንተ ከነዚህ የበለጡ ብዙ ምሳሌዎችን ልትጨምሩ ትችላላችሁ፡፡በእያንዳንዱ በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታዎች የምንወስዳቸው እንደ ጌታ ፈቃድ ያሉ ርምጃዎች ጌታችን እንዲከብርና እንዲታይ ያደርገዋል፡፡ጌታ ኢየሱስም “መስቀል መሸከም” ብሎ የሚናገረው ስለ እንደዚህ ዓይነት ተመሳሳይ ርምጃዎች ነው፡፡ቢያምም የራስን ምርጫዎች ለሱ ክብር መተው! ቢያምም ረጅሙንና ፈታኙን ጎዳና ከሱ ጋር ተስማምቶ መጠብጠብ!

ከላይ ከጠቀስኳቸው ፈተናዎች ጠንከር ያሉ ብዙ ፈታኝ መከራዎችና መንገላታቶች ሊመጡ ይችላሉ፡፡እነዚህ ክስተቶች በየትኛውም መንገድ ወደ እኛ ይምጡ ውስጣችንን የሚፈትሹ ለመሆናቸው ምንም ጥርጥር ሊገባን አይገባም፤ጌታ ላይ መደገፋችንንና አለመደገፋችንን ይመሰክራሉና፡፡

በእንደዚህ ዓይነት ጊዜያት ከጫናው የተነሣ ስፍራችንን ሳንለቅ፣በጌታ ፊት በመሆን፣ጸጋን በመለመንና ለሥጋችን የሚመቸውን አካሄድ ሳንመርጥ፣እንደ ጌታ ፈቃድ በመሄድ እሱን በሕይወታችን ማሳየት ትልቅ አስተዋይነት ነው፡፡ከዛ ፈተና ስንወጣም የሚኖረን ምስክርነት ጠንካራ ይሆናል፡፡

ሰይጣን ይህ እንዳይሆንና እንደ ጴጥሮስ ዓይነት ለስጋ የሚመቹ አቋራጮችን ያሳየናል፣ያቀርባልም፡፡ስለዚህ በመንፈስ እያስተዋልን፣ “ወደ ኋላዬ ሂድ አንተ ሰይጣን የሰውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብም”(ማቴዎስ 16፡23) ልንለው ይገባል፡፡

ጌታ ይርዳን!
Bekele Belachew
Write a comment...

Monday, August 17, 2015

አዲስ ራእይ ያስፈልገናል (Fresh vision)



ነቢዩ ኢሳይያስ በሱ ዘመን ከነበሩ የእግዚአብሔርን ሕግ በማወቅ በጽድቅና በቅድስና ከሄዱ ሰዎች መካከል አንዱ እንደ ነበር በጻፋቸው እጅግ በርከት ባሉት ትንቢታዊ መልእክቶቹ ላይ ይስተዋላል ፡፡

 
ነቢዩ ኢሳይያስ እግዚአብሔርን የሚፈራና የሚያውቅ ሰው በመሆኑ ከሱ ፈቃድ ባፈነገጠ ኑሮ የሚሄዱ እስራኤላውያንን ወደ መስመር እንዲገቡ ከበድ ያለ ተግሣጽ ያለው መልእክት ሲያስተላልፍ እንደ ነበረ የትንቢት ኢሳይያስ መጽሐፍ ከምዕራፍ አንድ እስከ አምስተኛ ምዕራፍ ያሉት ክፍሎችን ስናነብ እንገነዘባለን፡፡

 
ስካርን የሚከተሉትን፣አምላካቸውን የማያውቁትን፣ትዕቢተኞችን፣በደልን በምናምንቴ ገመድና ኃጢአትን በሠረገላ ማሠሪያ ወደ ራሳቸው የሚስቡትን፣ክፉውን መልካም እና መልካሙን ክፉ የሚሉትን፣በዓይናቸው ጥበበኞችና በነፍሳቸው አስተዋዮች የሆኑ የመሰላቸውን(ኢሳይያስ 5) ወዘተ ወዮላችሁ እያለ ሲያስጠነቅቅ ከርሞ፣በስድስተኛው ምዕራፍ ላይ ከዚህ በፊት አይቶት የማያውቀውን ከፍ ያለ አስደንጋጭ ራእይ አየ፡፡ጌታ እግዚአብሔር ራሱን በሚገርምና በሚያስፈራ መልኩ ገለጠለት፡፡ያ አስደናቂና አስደንጋጭ ራእይ፣ኢሳይያስን ወደ ራሱና ወደ ውስጥ እንዲመለከት አድርጐታል፡፡ክስተቱ እጅግ አስደንግጦት ነበርና፣እንዲህ ነበር ያለው፡-

 
“ከንፈሮቼ የረከሱብኝ ሰው በመሆኔ ከንፈሮቻቸውም በረከሱባቸው ሕዝብ መካከል በመቀመጤ ዓይኖቼ የሠራዊትን ጌታ ንጉሡን እግዚአብሔርን ስለ አዩ ጠፍቻለሁ ወዮልኝ” (ቁ.5)

 
ባጭሩ ወዮላችሁ ወደ ወዮልኝ ተቀየረ፡፡የሚገርም ነው፡፡በነገራችን ላይ “ጠፍቻለሁ” የሚለውን ቃል በእንግሊዝኛ መጽሐፍ ቅዱሶች ላይ ስመለከት “I am ruined” ወይም “I am undone” የሚሉ ትርጉሞችን እንደያዘ አይቻለሁ፡፡አር ሲ ስፕሮውል የሚባሉ የእግዚአብሔር ሰው ለዚህ ቃል ትክክለኛውና በጣም ተቀራራቢ የሆነው ትርጉም “I am undone” የሚለው እንደ ሆነ ባስተማሩት ትምህርታቸው ላይ ሰምቻለሁ፡፡ “ጠፍቻለሁ” የሚለው ቃል “አበቃልኝ አልተርፍም” እንደ ማለት ነውና፡፡
አዎ፣ነቢዩ ኢሳይያስ የነበረበት ሁኔታ የመጨረሻ የሚያርበተብት፣ግራ የሚያጋባና የሚያስጨንቅ ነበረ፡፡ከዚህም የተነሣ ይህ ነቢይ በብዙ ጥልቅ ንስሐ በጌታው ፊት ያሳለፈ ይመስለኛል፡፡እውነተኛ ጥልቅ ንስሐ ከባድ ነውና፣በብዙ ሕመም እንዳሳለፈ የሚጠቁመን ክፍል ቁ.6 ነው፡፡እንዲህ ይላል፡-

 
“ከሱራፌልም አንዱ እየበረረ ወደ እኔ መጣ፤በእጁም ከመሠዊያው በጉጠት የወሰደው ፍም ነበረ፡፡አፌንም ዳሰሰበት”(ቁ.6)

 
ከንፈራችን በጣም ስስና በቀላሉ የሚጐዳ የአካል ክፍላችን እንደ ሆነ ይታወቃል፡፡እዚሁ ክፍል ላይ ነው በጉጠት የነበረው ፍም ያረፈው፡፡እጅግ በጣም እንደሚያም መገመቱ ከባድ አይሆንም፡፡አዎ፣ይህ ሕመም ትክክለኛና እውነተኛ ንስሐ ዋዛ እንዳልሆነ ይጠቁማል፡፡በዚያ የጋለ ጉጠት ላይ በነበረው ፍም ከንፈሩ ከተዳሰሰ በኋላ ነበረ በደሉ የተሻረለት፤ኃጢአቱም የተሰረየለት(ቁ.7).ከዚያም “ማንን እልካለሁ? ማንስ ይሄድልናል?” (ቁ.8) ሲባል “እነሆኝ እኔን ላከኝ” ( ቁ.8) የሚል ትሕትና የተላበሰ ቋንቋ  ከአንደበቱ ወጣ፡፡


 
በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ያየናቸው ነቢያትና ጸሐፍት ክብሩን አይተው ደንግጠውና ተለውጠው ቀርተዋል፡፡እውነት ለመናገር በበኩሌ “እባክህ ተገለጥና ትንሽ አስደንግጠን” የሚል ጸሎትም እየዳዳኝ ነው፡፡ሐዋርያው ዮሐንስ የጌታን ክብር ሲያይ “ባየሁትም ጊዜ እንደ ሞተ ሰው ሆኜ ከእግሩ በታች ወደቅሁ” (ዮሐንስ 1፡17)ብሎ ተናግሯል፡፡ነቢዩ ዳንኤል እግዚአብሔርን በክብሩ ሲያየው“ኃይልም አልቀረልኝም፤ደም ግባቴም ወደ ማሸብሸብ ተለወጠብኝ፤ኃይልም አጣሁ፡፡የቃሉንም ድምፅ ሰማሁ፤የቃሉንም ድምፅ በሰማሁ ጊዜ ደንግጬ በምድር ላይ በግምባሬ ተደፋሁ” (ዳንኤል 10፡8-9) ብሏል፡፡ነቢዩ ሕዝቅኤል ያንን አስገራሚ የእግዚአብሔር ክብር ምሳሌ ሲመለከት፣ “ባየሁም ጊዜ በግምባሬ ተደፋሁ”(ሕዝቅኤል 1፡28) ብሎ ነበር ክስተቱን የገለጸው፡፡ነቢዩ ዕንባቆ የእግዚአብሔር ክብር መምጣቱን በመንፈሱ አውቆ የተናገረው ነገር እጅግ ያስደንቀኛል፡፡እንዲህ ነበር ያለው፡-

 
“እኔ ሰምቻለሁ፣ልቤም ደነገጠብኝ፤ከድምፁ የተነሣ ከንፈሮቼ ተንቀጠቀጡ፤መንቀጥቀጥ ወደ አጥንቶቼ ውስጥ ገባ፤በስፍራዬ ሆኜ ተናወጥሁ” (ዕንባቆ 3፡16)

 
የእግዚአብሔር ሰማያዊ ጉብኝት አስደናቂም አስፈሪም ነው፡፡እኔ ሳስበው፣እግዚአብሔርን የተዳፈርንበትና ኃጢአትን አቅለን ያየንበት ምክንያት፣ጌታን በትክክል ስላልተረዳነውና በዚህ መልኩ(ትንሽም ቢሆን) በመንፈስ ሰላላየነው ይመስለኛል፡፡ታዲያ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል ? ብናየው ሁኔታዎች ይቀየራሉ የሚል እሳቤ አለኝ፡፡

 
የሚያገለግሉንና የሚያስተምሩን ሰዎች እግዚአብሔርን በእንደዚህ ዓይነቱ ሁኔታ (በትንሹም ቢሆን) ያላዩ ሰዎች ስለሆኑ፣ትክክለኛው የጌታችን ስዕል በብዙዎቻችን ዘንድ ጠፍቶብናል፡፡ስለዚህም እግዚአብሔርን መፍራት ከየት ይመጣል? ለዚህም ነው ብዙ ያገጠጡ ችግሮች በመካከላችን የሚታዩት፡፡

 
በግሌ በራሴ ሕይወት ደጋግሜ ማፈሬን አልደብቃችሁም፡፡እግዚአብሔርን እንደሚገባኝ አለመፍራቴን መንፈስ ቅዱስና ሕሊዬ ይመሰክሩልኛል፡፡የቅርብ ጊዜ ጸሎቴም እሱን በሚገባ መፍራት ወደ ሕይወቴ እንዲመጣ ነው፡፡ዋናውን ጥሎ ወደ የት ?

 
የእግዚአብሔርን ክብር ያዩ ሰዎች በሕይወታቸው ትልቅ ለውጥ እንደነበራቸው መጽሐፍ ቅዱስ በተለያዩ ቦታዎች ተርኮልናል፡፡ሐዋርያው ጳውሎስ በሚያስደነግጥና በሚያስገርም ጉብኝት ነበር ወደ ጌታው የተመለሰው(ሐ.ሥራ 9፡1-9)፡፡ለዚህም ነው “በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ መዳናችሁን ፈጽሙ”(ፊሊጵስዩስ 2፡12) ብሎ የመከረን፡፡

 
የእግዚአብሔር ቃል “ልጆቼ ኑ ስሙኝ እግዚአብሔርን መፍራት አስተምራችኋለሁ” (መዝሙር 34፡11) ይላል፡፡አዎ፣እግዚአብሔርን በመፍራትና በመንቀጥቀጥ ለማክበርና ለመገዛት፣ቀርበነው ከራሱ መማር ያስፈልገናል፡፡በጽኑ ጸሎት ፊቱን መፈለግ ይኖርብናል፡፡ከቃሉ ጋርም ጠንከር ያለ ቁርኝት ያስፈልገናል፡፡መንገዱ ይኸው ነው--ቀርቦ ማወቅ(relational knowledge)! ስለዚህ ጌታ አዲስ ራእይ፣አዲስ ዕይታ፣አዲስ ማስተዋልና አዲስ ምልከታ እንዲሰጠን ፊቱን እንፈልግ!