Saturday, November 15, 2014

የመንፈሳዊ ራብ በረከት



የመንፈሳዊ ራብ በረከት

መንፈሳዊ ራብ ጌታን መናፈቅን፣እሱን ለማግኘት መጓጓትን፣ወደ እሱ ለመጠጋት ማሰብን ወዘተ ያመለክታል፡፡

በግለሰብ ይሁን በወል ደረጃ መንፈሳዊ ራብና ጥማት ለእግዚአብሔር መለኮታዊ ጉብኝት እጅግ ወሳኝ ናቸው፡፡አውነተኛ የሆነ መንፈሳዊ ራብና ጥማት እግዚአብሔርን እንድንሻው፣እንድንፈልገውና እንድንጠጋው ኃይል ይሆኑናል፡፡ ቃሉ “ጽድቅን የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው” (ማቴዎስ 5፡6) የሚለን ለዚህ ነው፡፡ “ብፁዓን” የሚለውን ቃል ድረ-ገጽ ላይ ያገኘሁት አምሊፋይድ መጽሐፍ ቅዱስ ደስተኞች፣በመንፈስ ባለጸጋ የሆኑ፣የረኩ፣የተባረኩ ወዘተ ብሎ ነው የሚገልጸው፡፡በነዚህ ቃሎችም መንፈሳዊ ራብ ሊያመጣ የሚችለውን የበረከት ሰፊነት ተገንዝቤአለሁ፡፡

ሐና መንፈሳዊ ራብ ያላቸው ሰዎች በጌታ ፊት ዋጋ ያላቸውና የማይረሱ እንደ ሆነ ስትናገር “ተርበው የነበሩ ከራብ አርፈዋል” (1 ሳሙኤል 2:5) ብላለች፤ አምላኳ የሚያረካ፣የሚያጠግብና የሚያሳርፍ መሆኑን በማወደስ፡፡

መንፈሳዊ ራብ በራሱ ትልቅ በረከት ነው፤ወደ ፊት እንድንዘረጋ፣እንድንቃትት፣ፊቱን አንድንፈልግ ያደርገናል፡፡የምር የሆነ መንፈሳዊ ራብ የሚመነጨው ደግሞ ያለንበትን ሁኔታ የእግዚአብሔር መንፈስ ሲያሳየንና ያለንበትን አዘቅት ስንጠላው ነው፡፡መንፈሳዊ ራብ ይጐተጉተናል፣አያስተኛንም፤ቃሉ“የሠራተኛ ራብ ለርሱ ይሠራል አፉ ይጐተጉተዋል” (ምሳሌ 16፡26) ይላልና ፡፡“ለርሱ ይሠራል” የሚለውን አስምሩልኝ፡፡ለማን? ለርሱ! አያስተኛውማ! ሳያገኝ አያሳርፈውማ! ለዚህ ነው መንፈሳዊ ራብ በራሱ የሚጓጓለት በረከት የሆነው፡፡

መንፈሳዊ ራብ ልክ እንደ ኤርምያስ ጌታን በትጋት እንድንፈልገው ያደርገናል፡፡ኤርምያስ ከብዙ ፍለጋ በኋላ ሕይወት የሚሰጠውን፣መንፈስ የሆነውን፣የጊዜውን ቃል ሲያገኝ እንዲህ ብሎ ተናገረ፡-

“ቃልህ ተገኝቷል እኔም በልቼዋለሁ፤አቤቱ የሠራዊት ጌታ ሆይ በስምህ ተጠርቻለሁና ቃል ሐሤትና የልብ ደስታ ሆነኝ” (ኤርምያስ 15፡16)

ከዚህ ምንባብ በጥቂቱ እንደምንረዳው፣ኤርምያስ ቃሉን በትጋትና በተራበ መንፈስ ሲፈልግ የቆየ ይመስላል፡፡ባገኘውም ጊዜ ከነበረው ናፍቆት የተነሣ ለመብላት ፋታ ያገኘም አይመስልም፡፡እናም እስከሚረካና በሐሤት እስኪጥለቀለቅ ድረስ በላው፡፡

ንጉሥ ዳዊት እውነተኛ መንፈሳዊ ራብ ያላቸውን ሰዎች እግዚአብሔር እንዴት እንደሚባርክ ሲገልጽ፣ የተራበችን ነፍስ አጥግቦአልና፤የተራቈተችንም ነፍስ በበረከት ሞልቶአልና (መዝ 107፡9) ብሎ ተናግሯል፡፡አዎ መንፈሳዊ ራብ የገባበት ሰው ሲቆፍር፣ሲፈልግ፣ሲቃትት ወዘተ ያድራል፤ዕረፍት አይኖረውም ያንን ራብ ሳያስታግስ፡፡ራቡ ጐትጓች ነውና፣አያስተኛውምና፡፡

ይህን መንፈሳዊ ራብ የሚያቀጣጥሉ ሦስት የታወቁ ነገሮች አሉ፡፡እነሱም፡-

  • የአግዚአብሔር ቃል አብዝቶ ማጥናትና ማሰላሰል
  • ደጋግሞ ለረጅም ጊዜ መጾም
  • በጌታ ፊት በውሳኔ መውደቅ

ጌታ እንደ ተስፋ ቃሉ መንፈሳዊን ነገር በሚራቡና በሚጠሙ ሰዎች ሕይወት፣ ከብዙ መሻት በኋላ ሲገለጥ አስደናቂ ነገር የሚሆነው፡፡ለዚህ ነው ሰፋ ካለ መንፈሳዊ መነቃቃት በፊት በቤተ ክርስትያን እርሱን የሚራቡና የሚጠሙ፣እናም በጓዳ እሱን የሚሹና የሚፈልጉ ሰዎች አስቀድሞ የሚያስነሣው፡፡

አንድ ክርስትያን ይህ ራብ በውስጡ ለረጅም ጊዜ ከጠፋ፣ለመውደቅ እየተንሸራተተ እንደ ሆነ ሊያስብ ይገባዋል የሚል አመለካከት አለኝ፡፡በግሌ ይህ ራብ ከውስጤ ሲጠፋ ግራ ይገባኛል፡፡እናም ሁሉን ነገር አቁሜ ወደ ቦታዬ ለመመለስ ብዙ ነገሮች አደርጋለሁ፡፡ከወትሮውም ብዙ እጸልያለሁ፤ብዙ መንፈሳዊ መጽሐፍትን በማንበብ ራሴን አነቃቃለሁ፤እንዳስፈላጊነቱም ጾምንም እጨምራለሁ፡፡

በጌታ ቤት በቆየሁበት ዘመን መንፈሳዊ ራብ የሚያስደንቅ ኡደት (positive cycle) እንዳለው ተገንዝቤአለሁ፡፡መንፈሳዊ ራቡ ልባችንን ባሰፋነው መጠን ያድጋል፡፡ አብዝተን እንድንቃትት ያደርገናል፡፡አብዝተን ስንጸልይ ደግሞ ጸሎቱ ሌላ ከፍ ያለ መንፈሳዊ ራብን ይወልዳል፡፡የሚመጣው መንፈሳዊ ራብ ደግሞ አብዝተን እንድንጸልይ ያደርገናል፡፡ወገኖቼ አንዱ አንዱን እየጨመረ ማብቂያ የሌለው አስደናቂ ነገር ውስጥ ነው የምንገባው፤እኛ በሥጋዊ አካሄዶች መንፈስን እስካላጠፋን ድረስ፡፡

ጌታ ሆይ ከፍ ያለ አንተን የሚሻና የሚፈልግ ልብ ስጠን !  

3 comments:

  1. በጣም ጥሩ መልዕክት ነው፡፡ በርትተህ ቀጥል፡፡ ጌታ ይባርክህ፡፡

    ReplyDelete
  2. Thank you Tesfahun ,God bless you for your comment.

    ReplyDelete
  3. ጌታ ይባርክ ዋው! አስደናቅ መንፈሳም መልዕክት ነው::

    ReplyDelete