Saturday, November 8, 2014

የድብርት መድሐኒት



የድብርት መድሐኒት

በዓለማችን በተለይ በምዕራቡ ምድር እንደምናየው ብዙ ሰዎች በተለያዩ የአእምሮ በሽታዎች ሲጠቁ እናያለን፡፡ዋነኛው የአእምሮ ችግርም ድብርት (depression) እንደሆነ በዚህ ዙሪያ ጥናት ያደረጉ ጠበብቶች ይስማማሉ፡፡የድብርት (depression) መንስዔው እንደ ቦታው እና እንደ ሰዉ አይነትና አኗኗር ይለያያል፡፡ሁሉንም የሚያመሳስላቸው ግን የችግሩ ስሜቶች እና ምልክቶች ናቸው፡፡ማለትም ሁሉም ሰዎች ላይ ደስታ ማጣት እና ሐዘን ይኖራል መጠኑ ቢለያይም፡፡ይህ ችግር ጌታ ኢየሱስን የማያውቁ ሰዎችን ብቻ ሳይሆን እሱን በሚገባ የሚያውቁ ሰዎችን ላይ ሳይቀር ይስተዋላል፡፡አንድ መታወቅ ያለበት ነገር ጊዜያዊ ጭንቀት እና ድብርት ማንኛችንም ላይ በተለያየ ምክንያት ሊመጣ ይችላል፤ነገር ግን እላያችን ላይ ቤቱን ሰርቶ እንዲረጋጋ እና መጫወቻ እንዲያደርገን መፍቀድ የለብንም፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ ይህ ችግር ወደ ሕይወታችን እንዳይመጣ ጥሩ መከላከላያ መድሐኒት ያለው ሲሆን፣ይህ ችግር ካገኘንም በኋላ ባስተማማኝ ሁኔታ የምንወጣበት መፍትሔም በውስጡ ይዟል፡፡ ከቃሉ ጋር ትክክለኛ እና የጠለቀ ሕብረት ያለው ክርስትያን፣ዝቆ እና ቀድቶ የማይጨርሰው የደስታ ምንጭ እንዳለ እኔ በተግባር በሕይወቴ አይቻለሁና በድፍረት እመሰክራለሁ፡፡
ንጉሥ ዳዊት በእንደዚህ ነፍስን ግራ በሚያጋባ አጣብቂኝ እና ሐዘን ውስጥ ከማናችንም በላይ ያለፈ ሲሆን ችግሩን፣መፍትሔውንና የመፍትሔውን ውጤት በመዝ 42፡2-4  በሚደንቅ ሁኔታ ጽፎልናል፡፡ይህ ክፍል እጅግ ግሩም ትምሕርት ያዘለ ሲሆን፣ በሚገባ በሕይወታችን ከተገበርነው ትልቅ በረከት እንዳለው አምናለሁ፡፡ይህንን ምንባብ ወደ ጌታ ከመጣሁ በኋላ ከመቶ ጊዜ በላይ አንብቤዋለሁ፡፡አሁንም ደጋግሜ የማነበው ክፍል ነው፡፡እንዳውም በጸሎት ጊዜዬ ክፍሉን ወደ ራሴን እያስገባሁ የምጸልይበትም ጊዜ አለ ፡፡ቃሉ እንዲህ ይነበባል፡-

‹‹አንተ አምላኬ ኃይሌም ለምን ትተወኛለህ?ጠላቶቼ ሲያስጨንቁኝ ለምን አዝኜ እመላለሳለሁ?ብርሀንና እውነትህን ላክ እነርሱም ይምሩኝ ወደ ቅድስህናህ ተራራ እና ወደ ማደሪያህ ይውሰዱኝ፡፡ወደ እግዚአብሔር መሰዊያ ጎልማስነቴንም ደስ ወዳሰኛት ወደ አምላኬ እገባለሁ››

ንጉሥ ዳዊት በእንደዚህ ዓይነት ሁኔታ የቆየበት ጊዜ ባይታወቅም ትንሽ እንደቆየ መገመት ይቻላል፡፡ይህንን የሚጠቁመን ‹‹ለምን አዝኜ እመላለሳለሁ››የሚለው ሐሳብ ነው፡፡እንደዚህ ዓይነት በደል፣ሐዘንና ጭንቀት የሚያደርሱበት ደግሞ ጠላቶቹ(አጋንንቶች-የሰው ጠላት የለንምና)እንደሆኑ ይናገራል፡፡ከዚያም መፍትሔውን ራሱ ያቀርባል እንዲህ ብሎ ‹‹ብርሃንህንና እውነትህን ላክ››፡፡በዚህ ሐረግ ዳዊት መፍትሔው ከእግዚአብሔር አፍ የሚወጣ ቃል እንደሆነ ነው የሚነግረን፡፡ባጭሩ ክፍሉ በጸሎት መንፈስ ሆነን ፊቱን እየፈለግን፣እየቃተትን፣ቃሉን እያሰላሰልን በጽናት ስንጠብቀው መድሐኒት እንደሚላክልን ይጠቁመናል፡፡ዳዊት ክፋት ወደሌለበት ‹‹ወደ ቅድስና ተራራውና ወደ ሕልውናው (His presence)›› ደጋግሞ ሄዶ ተሰውሮ ያውቃልና፣ያንን በመሻትና በመጠማት ነው አምላኩን እየተማጸነ ያለው፡፡እንደምናውቀው በሕልውናው ውስጥ ደግሞ ሰላም አለ፤ደስታ አለ፤እረፍት አለ፤መረጋጋት አለ፡፡በሱ ፊት ጨለማ መቆም አይችልምና፣ትካዜና ሐዘንም ይሸሻሉ፡፡እኔም ይህንን ደጋግሜ በሕይወቴ ስላየሁኝ ሕያው ምስክር ነኝ፡፡ክርስትናን ውብና ልዩ የሚያደርገው ታዲያ ሌላ ምንድነው ?

ስለዚህ በራሳችን መታገል ስለማይጠቅመን፣ያንን አቁመን ሙሉ በሙሉ ራሳችንን ለእሱ እንስጠውና በፊቱ እንውደቅ! “በመመለስና በማረፍ እንድናለንና በጸጥታና በመታመን (በፊቱ በመሆን) ኃይል ይሆንልናልና” (ኢሳይያስ 30፡15 አጽንዖት የእኔ) መጥተን በፊቱ ምንም ሳናቅማማ እንረፍ!

No comments:

Post a Comment