Saturday, December 21, 2013

የሚሰማ ጸሎት(genuine prayer)




የሚሰማ ጸሎት(genuine prayer)


በምድር ላይ እኛ ክርስትያኖች በተለያየ ቋንቋ ወደ አምላካችን ጸሎትን እናቀርባለን፡፡በጌታችን ፊት የማይቀርብ የጸሎት አይነት የለም፡፡መጸለያችን ሳይሆን እግዚአብሔር የልብ አምላክ ነውና፤ምሳ 212፡- ‹‹የሰው መንገድ ሁሉ በዓይኑ ፊት የቀናች ትመስለዋለች እግዚአብሔር ግን ልብን ይመዝናልእንደሚል የምንጸልይበት የልብ ይዘት(motive) በእግዚአብሔር ዘንድ ይመዘናል፡፡ዋናው ቁም ነገር መጸለያችንና ፎርማሊቲ ማሟላታችን ሳይሆን በእርሱ ፊት ሞገስ ያገኘ ጸሎት መጸለያችን ነው ፡፡ማለቴም ሰውን ልናታልልና ልናስመስል እንችል ይሆናል ብሎም የጸሎት ሰዎች ሁሉ ልንባል እንችላለን ነገር ግን እግዚአብሔር ፍጹም አይታለልምና፤በእርሱ ፊት ፍጥረት ሁሉ የተገለጠ እና የተራቆተ ነውና(እብ 413) ጸሎታችን ጣራ ላያልፍ ይችላል፡፡

1ዮሀ 321-22 ጸሎታችን እንዲሰማ ካስፈለገ ልናደርጋቸው የሚገቡን ሁለት መርሆዎችን የያዘ ቃል ነውና ልጥቀሰው፡፡እንዲህ ይላል -‹‹ወዳጆች ሆይ ልባችንስ ባይፈርድብን በእግዚአብሔር ዘንድ ድፍረት አለን፤ትእዛዙንም የምንጠብቅና በፊቱ ደስ የሚያሰኘውን የምናደርግ ስለ ሆንን የምንለምነውን ከእርሱ እናገኛለን፡፡››አዎ ትእዛዙን መጠበቅ እና በፊቱ ደስ የሚያሰኘውን ማድረግ ቅድመ ሁኔታዎች ናቸው ጸሎታችን እንዲሰማ ካስፈለገ፡፡እንደ ፈለግን እየሆንን ልባችን በምናደርጋቸው ስህተቶች እየፈረደብንና በሀጢያት ክስ ውስጣችን እየታመሰ የምንጸልያቸው ጸሎቶች በፍጹም እንደማይሰሙ ነው የሚነግረን፡፡

የሚሰማ ጸሎት ምን አይነት ነው የሚለውን ጥያቄ በጥሩ መልኩ ሊመልስልን የሚችል ቃል  መዝ 171-4 እና 15 ላይ እናገኛለን፡፡ይህ መዝሙር ሲጀምርየዳዊት ጸሎትብሎ ነው የሚጀምረው፡፡ዳዊት እግዚአብሔርን በሚገባ ያውቅ የነበረ ሰው ስለነበር ጸሎት ምን አይነት መሆን እንዳለበት ጠንቅቆ ያውቅ ነበር፡፡መዝ 171-4 ላይ ያለውን ዘርዝሬ ሳስቀምጥ የሚሰማ ጸሎት የሚከተሉትን መርሆዎች እንደሚፈልግ እርግጠኛ ነኝ፡፡እነርሱም፡-

1ኛ፡-በተንኮለኛ ከንፈር ያልሆነ ጸሎት(ቁጥር 1)
2ኛ፡-በጌታ ፊት ንጹህ ልብ (ቁጥር 3)
3ኛ፡-በሰው ጉዳይ የማይቀባጥር የህይወት ምልልስ(ቁጥር 4)
4ኛ፡-ጭንቅ የሆኑ መንገዶቹን ለመጠበቅ የጨከነ ማንነት (ቁጥር 4)
5ኛ፡-በጽድቅ ፊቱን የሚያይ ህይወት(ቁጥር 15)-ይህ መርህ 1 እስከ 4 ያሉትን ያቅፋል

ዳዊት እነዚህን መርሆዎች አሟልቶ ነው ቁጥር 6 ላይ ‹‹ጆሮህን ወደ እኔ አዘንብል ቃሌንም ስማ››ብሎ የጸለየው፡፡በዚህ ቃል ሲታይ የብዙዎቻችን ህይወትና አረማመድ ብዙ የሚጎድለው ይመስለኛል፡፡እነዚህ ከላይ የተዘረዘሩት አምስቱ ነጥቦች ለጸሎታችን ዋና ማገር እንደሆኑም ልናስብ ይገባናል፡፡ስለዚህ ልመናን እና ምልጃን ከማቅረባችን በፊት በጌታ ፊት ያልተስተካከለና የተበላሸ ነገር ካለ ለጌታ ልብን በመክፈት በሚገባ ልናስተካከልና ልንጸዳ(1ዮሀ 19)ይገባናል ብዬ አምናለሁ፡፡የሚቀጥሉት ሶስት እርምጃዎችም ወሳኝ ናቸው፡-
  • መናዘዝ (confession)
  • ሙሉ በሙሉ መመለስ (repentance)
  • ወደ ኋላ ላለመመለስ መጽናት (perseverance)
እነዚህን እርምጃዎች በትክክል ወስደን ህይወታችን ስናስተካክል ብቻ ነው ጸሎታችን የሚመለሰው ብሎም ጌታን የማየትና ክብሩንም አይተን የመጥገብ እድል የሚኖረን፡፡መዝ 6616-20 ላይም ተመሳሳይ ሀሳብ ያለው ነገር ተጽፎልናል፡፡እንዲህ ይላል፡-‹‹እግዚአብሔርን የምትፈሩት ሁሉ ስሙኝ፤ ለነፍሴ ያደረገላትን ልንገራችሁ።በአፌ ወደ እርሱ ጮኽሁ በአንደበቴም አመሰገንሁት።በልቤስ በደልን አይቼ ብሆን ጌታ አይሰማኝም ነበር።ስለዚህ እግዚአብሔር ሰማኝ፤ የልመናዬን ድምፅ አደመጠ።ጸሎቴን ያልከለከለኝ ምሕረቱንም ከእኔ ያላራቀ እግዚአብሔር ይመስገን።››እጅግ አስደናቂ ቃል ነው፡፡ዳዊት ጸሎቱ ያልተከለከለበትን ሚስጥር ቁጥር 18 ላይ አስቀምጦልና እንዲህ ብሎ፡-‹‹በደልን በልቤስ አይቼ ብሆን ጌታ አይሰማኝም ነበር››ይህንን ጥቅስ የእንግሊዝኛ መጽሀፍ ቅዱስ(ESV)እንዲህ ነው የሚለው፡-
                ‹‹If I had cherished iniquity in my heart ,the Lord would not have listened››
‹‹cherish›› የሚለው የእንግሊዝኛ ቃል ትርጉም አቅፎ መያዝ፣ደብቆ ማቆየት፣ጠብቆ መያዝ ወዘተ የሚል ሀሳብ ያለው ሲሆንና ቃሉ ሳንናዘዝ ውስጣችን ደብቀን የያዝነውን በደል የሚጠቁም ሲሆን ወይም ደጋግመንም ርምጃ ሳንወስድበት የቆየም ሊሆን እንደሚችል ነው የሚያሳየን፡፡እናም እንደሚከተለው አብራርቶ መተርጎም የሚቻል ይመስለኛል፡-‹‹በልቤ በደልን ደብቄ/አቅፌ/ይዤ ቢሆን ጌታ አይሰማኝም ነበር››ስለዚህ በጌታ ፊት በደልንና ሀጢያትን ሳንናዘዝና በሚገባ ከህይወታችን ሳናስወግድ ጌታ አይሰማንም ማለት ነው፡፡


ያዕቆብ 43 ላይ ደግሞ ሌላ ጸሎታችን ላይሰማና ሊከለከል የሚችልበትን ምክንያት እናገኛለን እንዲህ በማለት፡-‹‹በምቾቶቻችሁ ትከፍሉ ዘንድ በክፉ ትለምናላችሁና አትቀበሉም››በዚህ ቃል ብርሀን ሲታይና ብዙው ጸሎታችን ስረ መሰረቱ ሲፈተሽ ከስስት፣ከራስ ወዳድነት እና ከክፋት ጋር የተያያዘ በመሆኑ ጸሎታችን ከጣራ አያልፍም፡፡ስለዚህ አንድ ጸሎት ስንጸልይ ሶስት ነገሮችን መጠየቅ አግባብነት አለው ብዬ አምናለሁ፡፡እነርሱም፡-

  • የሚጸለይበት ጉዳይ ለእግዚአብሔር ክብር ይሆናል ወይ ?
  • እንደ እግዚአብሔር ቃል ነው ወይ የጸለይኩት ?
  • ልቤን የሚፈርድብኝ ጉዳይና ክስ የለም ወይ?  
  
ብዙ ጊዜ የምንጠይቃቸው ነገሮች ረዘም ያለ ውጤት(long term effect) ስለሚኖራቸው በጥንቃቄ ማሰብም መልካም ነው፡፡አንዳንዴ የምንጠይቀውን ባለማወቅ ጌታን ስናስቸግር የፈለግነውን አግኝተን ህይወታችን ሊጎዳም ይችላል መዝ 10615 ላይ እንዲህ እንደሚል፡-‹‹የለመኑትን ሰጣቸው ለነፍሳቸው ግን ክሳትን ላከ››


በመጨረሻም ነገሬን ለመቋጨት ጸሎታችን እንዲሰማ ካስፈለገ ልናደርግ የሚገቡንን ተግባራዊ ነገሮች አስቀምጬ እጨርሳለሁ፡-
  • ጸሎታችን ከስስት ከራስ ወዳድነት እና ከክፋት የጸዳ ለመሆኑ ልብን በሚገባ መፈተሸ እጅግ መልካም ነው
  • በልባችን እየተንገዋለለ በጥሩ ሁኔታ ሳንናዘዝ እያድበሰበስን የያዝነው ሀጢያት ካለ በሚገባ መናዘዝ ይገባናል ምሳ 2813 ላይ እንዲህ እንደሚል፡- ‹‹ሀጢያቱን የሚሰውር አይለማም የሚናዘዝባትና የሚተዋት ግን ምህረትን ይቀበላል››
             ‹‹አይለማም››የሚለው ሃሳብ በዚህ የመልእክት አውድ ‹‹ጸሎቱ መልስ አያገኝም ወይም ጸሎቱ አይሰማም›› የሚል ትርጉም ሊኖረው ይችላል
  • ጭንቅ የሆኑ መንገዶቹን ለመከተል በሚገባ መጨከን ይገባናል
ጌታ ይርዳን!!









No comments:

Post a Comment