Wednesday, January 1, 2014

ለነፍሴ ያደረገላትን ልንገራችሁ



ለነፍሴ ያደረገላትን ልንገራችሁ

ጌታን እንደ ግል አዳኜ አድርጌ ከመቀበሌና መሪ አድርጌ ከመሾሜ በፊት ህይወቴ እንደ አይን የጠፋና የተበላሸ ነበር፡፡ሀይለኛ የሱስ ቀንበር እላዬ ላይ ነበርና የየቀኑ ኑሮዬ የስቃይና የመከራ ነበር፡፡መጠጣት ነበረብኝ፤መቃም ነበረብኝ፤ማጨስ ነበረብኝ፡፡ከዚህም የተነሳ ማህበራዊ ህይወቴ የተበላሸ ነበር፡፡

የክፉ ተጽእኖ እንደ ነበር በሕይወቴ ቅንጣት አልጠራጠርም፡፡አሁን ላይ ቆሜ ሳየው ባሁኑ ሰአት መኖሬ እራሱ ተአምር ነው፡፡ሞቴ ይፈጥናል የሚል ግምት በኔም በአቅራቢያ ባሉ ሰዎች ሁሉ የሚታሰብ ጉዳይ ነበር፡፡እንደዚህ አይነቱ ህይወት ከ 15 አመት በላይ አሸኝ፡፡ከዚህ ስቃይ ገፍትሮ ለመውጣት ብሞክርም ‹‹ታጥቦ ጭቃ›› አይነት ኑሮ ለረጅም ዘመን ገፋሁ፡፡ውስጤ ስቃይ ነበር፤ለቅሶ ነበር፤ሀዘን ነበር፤ተስፋ መቁረጥ ነበር፤ሞትን በሀይል መመኘት ሁሉ ነበር፡፡

እያንዳንዱን ቀን በመጠጥ ለመሰወር የመጠጥ ባሪያ ብሆንም እንዳውም የነበሩብኝ ውስብስብ ችግሮች እየገጠጡ መጡ፡፡ችግሮቹን የሚያባብሱ ሰዎች ነበሩ፤እኔም አባብሰው ነበር፤የነበርኩበት ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሁኔታዎች ያባብሱት ነበር፡፡ስለዚህ በአጭር ቃል ረግረግ ጭቃ ውስጥ (መዝ 40፡2) ነበርሁ ማለት ይቻላል፡፡


የዘወትር የውስጥ ስቃዬና ጩኸቴ ‹‹ማን ያወጣኛል›› የሚል ነበር፡፡ወደ ቤ/ክ በጣም አልፎ አልፎ ሄጄ ከነበርኩበት ጉድ ለመውጣት ብሞክርም ውስጤ በሚገባ ስላልተለወጠ ታይታዊ የሆኑ ጊዜያዊ ለውጦች ስለ ነበሩ አንድ መጥፎ ክስተት ሲገጥመኝ የነበረኝ የሱስ ቀንበር እጥፍ ድርብ ያገረሽ ነበር፡፡

ከላይ በጠቀስኳቸው ውስብስብ ሁኔታዎቸ ሁሉ ነገሬ ተበላሽቶ በቃልኝ ከዚህ በኃላ ሰው አልሆንም፤ዳግመኛ አልነሳም ፤ብሩህ ቀናትን አላይም ብዬ ደመደምኩ፡፡ዘመድ፣ወዳጅና ቤተሰብ ሁሉ ራቀኝ፡፡መዝ 31፡2 ላይ ‹‹እንደ ሞተ ሰው ከልብ ተረሳሁ፤እንደ ተበላሸ እቃም ሆንሁ›› የሚለው የመዝሙረኛው ዳዊት አገላለጽ በሚገባ የነበርኩበትን ማጥ የሚገልጸው ይመስለኛል፡፡በሰው ሁሉ ዘንድም ተረሳሁ፡፡


በእንደዚህ ውስብስብ ታሪክ ውስጥ እያለፍኩም ቢሆን የእግዚአብሔር ቃል በውስጤ ያለ ማቋረጥ ይዘራ ነበር፡፡ይህ ዘር በቅሎም ፍሬ ማፍሪያው በጌታ ጊዜ ደረሰ፡፡እናም ተስፋዬ ተሟጦ ውሀ የሚያጠጣኝ ዘመድ ወገን ሙሉ በሙሉ ሳጣ ወደ አምላኬ ሙሉ በሙሉ የመመለስ ጉዳይ በአንድ ድንቅዬ ቀን የዛሬ 15 አመት በግማሽ ቀን ገፍቶ አየለ፡፡በዚህ ውስጣዊ ትንቅንቅ እኔነቴ ለሁለት ተከፍሎ ትግል ሆነ፡፡ይሉኝታ፣የሰው ፍርሀት፣የሱስ ተጽእኖው እስራት፣የብቸኝነቱ መከራ ሁሉ እንደ ዛፍ እያወዛወዘኝ በሌላ በኩል ወደ እርሱ ብመለስ የማገኘውን እረፍት እያሰብኩ ለ 6 ሰአታት ያህል የታገልሁት ትግል በሕይወቴ አይረሳኝም፡፡

ወደ ልቤም ተመልሼ(ሉቃ 15:17) ስወስንና ከነገ ጀምሮ ወደ አባቴ ቤት እሄዳለሁ፤አለምን እክዳለሁ፤ሰይጣንንና አገዛዙን እክዳለሁ፤የስጋን መንገድ አልከተልም፤እስከ መጨረሻ የእርሱ ባሪያ እሆናለሁ ብዬ በልቤ ልክ ቃል ኪዳን ስገባ፡-

  • ቤቱ በብርሀን ተሞላ

  • የደስታ መንፈስ በውስጤ ፈሰሰ

  • ልዩ የሆነ የሰላም መንፈስ አጥለቀለቀኝ

  • ከጨለማ ወደ ብርሀን እንደ ተሸጋገርሁ ታወቀኝ(ቆላ 1፡14)

ከዚያ ድንቅ ውሳኔ በኃላ  የጫት፣የሲጋራ እና የመጠጥ ሱስና ቀንበር ባንድ ቀን ሙሉ በሙሉ ተሰበሩ፡፡የሚገርመው ነገር እነዚህን ሱሶች ባቆምኩ የመጀመሪያዎቹ ቀናትና ሳምንት ውስጥ እራስ ምታት እንኳን አልነበረኝም፡፡ይሄ ሁኔታ ሁልጊዜ ይገርመኛል፡፡ከዛ ሁሉ ቀንበር ተላልቄ የነጻነት አየር እየተነፈስሁ እነሆ አሁን 15 አመት አልፎኛል፡፡ኢሳ 61፡1-3 እንደሚል ፡-

  • ብዙ የልብ ስብራት ነበረኝ ተጠግኛለሁ

  • ምርኮኛ ነበርሁ ነጻ ሆኛለሁ

  • ታስሬ ነበር ተፈትቻለሁ

  • አለቅስ ነበር የደስታ መንፈስ በማያቋርጥ ሁኔታ በውስጤ ፈሷል

  • በአመድ  ፋንታ አክሊል በሀዘን ፋንታ የምስጋና መጎናጸፊያ ተደርቦልኛል

  • የጉዳቴ መጠን ትንሽ አልነበረም የካሳዬ ብዛትም ከአእምሮ በላይ ሆኗል

  • ብዙ ድንቅ ነገሮችን አሳየኝ ፡፡ህይወቴን በመንፈሱ ዘይት አለመለመው(መዝ 92፡10)፡፡


ስለዚህም እንዲህ ብዬ አንድ ህይወቴን በሚገባ በመግለጹ የምወደው መዝሙር አለና እንዲህ ብዬ አዜማለሁ፡-

         አየሁ ጌታዬ ከንዱን አንስቶ
         የጠላቴን ራስ ሲቀጠቅጠው
         እስራቴንም ሲበጣጥሰው
         ሞት ሞት የሸተተውን ህይወት
         በአዲስ መአዛ ሲለውጠው!!

እስቲ አንድ ጥያቄ ልጠይቃችሁና ምስክርነቴን ልቋጭ፡-
ለመሆኑ እርሱን የሚመስል ፈዋሽ፤አለምልሞ አድሶና አበርትቶ የሚያቆም ከወዴት ይገኛል?የተጣለንስ የሚያነሳ ማን ነው?
ለኔ መልሱ ፡-የለም ነው!!
እርሱ ብቻውን ከዘላለም እስከ ዘላለም የተባረከ ይሁን !!!!!!
ይህንን ምስክርነት በቅርብ ጊዜ በመጽሀፍ መልክ ላወጣው በቂ ዝግጅት እያደረግሁ ነውና ሙሉውን ታሪኬን ታነቡታላችሁ፡፡ተባረኩ!!

በቀለ በላቸው(ዶ/ር)
beke_abay@yahoo.com
240-330-5004





Jan 1,2014

እግዚአብሔርን ማወቅ



እግዚአብሔርን ማወቅ

እግዚአብሔርን ለማወቅ ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ወሳኝ ነው፡፡ያዕቆብ 4፡7 ላይ ‹‹ወደ እግዚአብሔር ቅረቡ ወደ እናንተም ይቀርባል›› የሚል ቀላል አባባል የሚመስል ግን የጠለቀ እውነት ያለውን ቃል እናገኛለን፡፡በዚህ ቃል ላይ የእኛ የልብ ተነሳሽነት እና የመቅረብ ፈቃደኝነት እንደሚቀድምም እናስተውላለን፡፡አዎ ወደ እግዚአብሔር በቀረብን ቁጥር ከእርሱ በምናገኘው ብርሀን መንፈሳዊውን አለም እየተረዳንና የእግዚአብሔር መለኮታዊ ማንነት እየተገለጠልንና ታላቅነቱ፣ገናናነቱ፣ሀያልነቱ እና ጥበቡ እየበራልን የምንድነቅበትና የምንገረምበት ህይወት ውስጥ እራሳችንን እናገኘዋለን፡፡ማለትም የማወቃችንን መጠን የመቅረባችንን ልክ ይወስነዋል፡፡


እግዚአብሔርን ማወቅ ስል ዝም ብሎ ስለ ቀለም እውቀት መናገሬ ሳይሆን በጸሎትና ከቃሉ ጋር በሚደረግ ህብረት እና ግንኙነት የሚገኝ እውቀትን (intimate relational knowledge) መናገሬ ነው፡፡ይህ አይነት መረዳት ብዙ ፊቱን በመፈለግና በቂ ጊዜ በመውሰድ የምናገኘው ነው፡፡ኤፌ 1፡17 ላይ ‹‹የክብር አባት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ክርስቶስን በማወቅ የጥበብንና የመገለጥን መንፈስን እንዲሰጣችሁ እለምናለሁ››በማለት ሀዋርያው ጳውሎስ የሚጸልየው ጸሎት አለ፡፡ማለትም የጥበብንና የመገለጥን መንፈስ የምናገኘው “ክርስቶስን በማወቅ” እንደሆነ ነው የሚነግረን፡፡“ክርስቶስን በማወቅ”የሚለው ቃል የጠለቀ ግንኙነትን (deeper intimacy) ነው የሚጠቁመን፡፡“ክርስቶስን በማወቅ” የጥበብና የመገለጥን መንፈስ ሲበዛልን ደግሞ የልባችን አይኖች እንደሚበሩና ሌሎች መረዳቶች እንደሚከተሉ ያስረዳናል፡፡ስለዚህ በዳር ዳር ወይም በነካ ነካ ሕይወት እግዚአብሔርን ማወቅ ሊታሰብ አይገባም፡፡ይልቁንም በጽኑነት ፊቱን መፈለግ ይገባል፡፡


እግዚአብሔርን ማወቅ ዋነኛ ነገር ነው፡፡የመንፈሳዊ በረከቶች ሁሉ ምንጭም ነው፡፡ኤር 9፡23-24 ላይ እርሱን በማወቅ ዙሪያ የተጻፈልን እጅግ ጥልቅ የሆነ ሚስጥር ያለው ቃል እናገኛለን፡፡እንዲህ ይነበባል፡-ጠቢብ በጥበብ አይመካ ኃያልም በኃይሉ አይመካ ባለ ጠጋም በብልጥግናው አይመካ ነገር ግን የሚመካው፡-ምህረትንና ፍርድን ጽድቅንም በምድር ላይ የማደርግ እኔ እግዚአብሔር መሆኔን በማወቁና በማስተዋሉ በዚህ ይመካ ደስ የሚያሰኙኝ እነዚህ ናቸውና ይላል እግዚአብሔር፡፡››ይህ ቃል እግዚአብሔርን በማወቅና በማስተዋል ሊኖረን ስለሚገባ ትምክህት ነው የሚናገረው፡፡አዎ እርሱን ስናውቅ የሚመጣ እምነት አለ፣መደገፍ አለ እራስን መስጠት አለ፡፡ይህ “እውቀትና ማስተዋል” ግን በቂ ጊዜን በፊቱ በማሳለፍ የሚመጣ ነው፡፡እንዲህ በማድረግም እኛን ብቻ ሳይሆን እግዚአብሔርንም እንደምናስደስት እንወቅ፡፡ባለም እንዳሉ እርሱን እንደማያውቁ ሰዎች በዚች አለም ጥበብ፣ሀይል እና ብልጥግና እንዳንመካም ያስገነዝበናል፤ለጊዜው ቢጠቅምም ጠፊና ሀላፊ ነውና!


ያለንበት ዘመን ከመቼውም ዘመን ይልቅ እርሱን ለማወቅ ለሚፈልግ ሰው እጅግ የተመቻቸ ይመስለኛል፡፡በተለያዩ መንገዶች የሰውን ልብ የሚነኩ ከመጽሀፍ ቅዱስ ጨምሮ ብዙ መንፈሳዊ መጽሀፍት አሉ፡፡በዙሪያችንም እግዚአብሔርን በህይወታቸው ያዩና መንፈሳዊውን አለም በሚገባ የተገነዘቡና ከጌታ የተማሩ ብዙ ሰዎች አሉልን፡፡ስለዚህ ቀናችን በችኮላ ሳያልቁ የዚህ የበረከት ተካፋይ ለመሆንና እርሱን ለማወቅ ይሉኝታን ሰብረን መነሳት አለብን ብዬ እመክራለሁ፡፡
በነገራችን ላይ እርሱን ማወቅ ቀላል ነው ብዬ አላስብም፤የምንከፍላቸው ብዙ ዋጋዎች ይኖራሉ፡፡ግን ይህ የሚሆነው ከብዙ ውስጣዊ ሰላምና ጸጥታ ጋር ነው፤በቀረብነው ቁጥር ህልውናው ያገኘናልና፡፡ለትምህርታችን የተጻፈ ፊሊ 3፡9-11 ላይ የሚገኝ ሀዋርያው ጳውሎስ ‹‹ክርስቶስን ለማወቅ›› የከፈለውን መስዋእትነት የሚገልጽ ግሩም መልእክት እናገኛለን፡፡እንዲህ በማለት፡-‹‹አዎን በእውነት ከሁሉ ይልቅ ስለሚበልጥ ስለ ክርስቶስ ኢየሱስ ስለ ጌታዬ እውቀት ነገር ሁሉ ጉዳት እንዲሆን እቆጥረዋለሁ፡፡ስለ እርሱ ሁሉን ተጎዳሁ ክርስቶስንም አገኝ ዘንድ በክርስቶስ በማመን ያለው ጽድቅ ማለት በእምነት ከእግዚአብሔር ዘንድ ያለው ጽድቅ እንጂ ከህግ ለእኔ ያለው ሳይሆንልኝ በእርሱ እገኝ ዘንድ ሁሉን እንደ ጉድፍ እቆጥራለሁ›› በዚህ በተጠቀሰው ቃል ላይ ሀዋርያው ጳውሎስ አላማ የነበረው(focused ) ሰው እንደ ነበረ እናያለን፡፡ሌላውን ነገር ሁሉ እንዲንቅ አቅም የሰጠው ሀይለኛ ብርሀንና መንፈሳዊ መረዳት እንደ ነበረ ምንም አያጠራጥርም፡፡ ሀዋርያው ጳውሎስ በህይወቱ መሰጠት የነበረው ሰው ሲሆን ቅዱስ አለመርካት (holy dissatisfaction)መገለጫ ባህርይውም ነበር፡፡ይህንን ህይወት ግን በብዙ ትጋት እንዳገኘው ልናስተውል ይገባናል፡፡የከፈላቸው ብዙ መስዋእቶች ነበሩ፡፡በእነዚያም በወሰዳቸው እርምጃዎች እና ጽናቱ እግዚአብሔርን ከሚገባው በላይ አውቋል፡፡በእኛም ህይወት እንዲህ ነው የሚሆነው፡፡ወደ እርሱ በቀረብን ቁጥር ማንነቱ እየገባንና እየተገለጠልንና ለሌሎች ነገሮች ያለን ዋጋና ክብር እያነሰና እርሱ ግን እየተለቀና እየላቀ ይመጣል፡፡


ጌታን አውቆ ሰው ድሮ እንደ ነበረው መሆን አይችልም፡፡ጌታን በማወቅ እምነታችን ያድጋል፣ደስታችን ይጨምራል፣ሰላማችን ይበዛል፣መረጋጋታችን ይልቃል ወዘተ፡፡ለአለም ያለን አመለካከት፣ለእራሳችን ያለን አመለካከት ፣ለሰዎች ያለን እይታ ወዘተ ሁሉ በሚገባ ይቀየራል፡፡ያካሄድ ለውጥ  ይመጣል፤ያስተሳሰብ ለውጥ ይመጣል፤የንግግር ለውጥ ይመጣል፤የምርጫ ለውጥ ይመጣል፤የእይታ ለውጥ ይመጣል፤ሌላም ሌላም!በጥቅሉ ብዙ ለውጦች ይመጣሉ፡፡እያንዳንዱም አዎንታዊ ለውጥ ለበለጠና ለጨመረ ለውጥ ይገፋፋናል እኛ ወደ ስጋዊ ነገር ተመልሰን እስካላቆምነው ድረስ፡፡
ሆሴ 6፡3 ላይ ‹‹እንወቅ እናውቀውም ዘንድ እግዚአብሔርን እንከተል እንደ ወገግታ ተዘጋጅቶም እናገኘዋለን›› የሚል እግዚአብሔርን ስለማወቅ የተጻፈ ድንቅ መርህ ያለው ቃል እናገኛለን፡፡እዚህ ቃል ላይ ሁለት ግልጽ ቁም ነገሮች ተቀምጠዋል፡፡እነርሱም፡-

1ኛ፡-የእግዚአብሔር ለመታወቅ ዝግጁነቱ

ጌታ እራሱን ለሰው ልጆች ለመግለጥ ዝግጁ ነው፡፡ፊሊ 4፡6 ላይ ይህንኑ የሚያጸና ቃል አለልን፡፡እርሱም ፡-‹‹ጌታ ቅርብ ነው››የሚል ነው፡፡አዎ ለማወቅ ለፈለገ ሰው ጌታ ከእስትንፋሳችን ይልቅ የቀረበ አምላክ ነው፡፡ይህንን ቃል በህይወቴ ስላየሁት በቂ ምስክር ነኝ፡፡ደግሜም እላለሁ፡-‹‹እጅግ ቅርብ ነው››በተለያዩ የመጽሀፍ ቅዱስ ክፍሎችም ለመታወቅ እጁ የተዘረጋ፤በብዙ ግብዣ እና ዝግጁነት የሚገኝ መሆኑን ተገልጾልናል፡፡ለአብነት ያህል ትንሽ የግብዣ ማስረጃዎችን ላቅርብ፡-
ማቴ 11፡28 ላይ ‹‹እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ ወደ እኔ ኑ››ብሎ ይጣራል

ምሳሌ 8፡4 ላይ ‹‹እናንተ ሰዎች እናንተን እጠራለሁ፤ድምጼም ወደ ሰዎች ልጆች ነው››የሚል ግልጽ መልእክትም አለን

ኢሳ 55፡1 ላይ ‹‹እናንተ የተጠማችሁ ሁሉ ወደ ውኃ ኑ፤ገንዘብም የሌላችሁ ኑና ግዙ ብሉም ኑ ያለ ገንዘብም ያለ ዋጋም የወይን ጠጅምና ወተት ግዙ››እያለ ወድ ወደ ሆነ ግን የተከፈለበት ነጻ ግብዣ ይጋብዘናል

ሮሜ 10፡21 ላይ ‹‹ቀኑን ሁሉ ወደማይታዘዝና ወደሚቃውም ሕዝብ እጆቼን ዘረጋሁ››በማለት አሁንም ዝግጁነቱን ይነግረናል

አዎ እጁ እንደተዘረጋች ነው፡፡ለመታወቅም እጅግ ዝግጁ ነው፡፡ስለዚህ የምናመካኘው ነገር አይኖረንም፡፡

2ኛ፡-እግዚአብሔርን ለማወቅ ‹‹መከተል›› ማስፈለጉ

“እንከተል” የሚለው ቃል ዲሲፕሊን የሚያስፈልገው፤ጽናትን የሚጠይቅ፤ትእግስትን የሚሻ፤ንቁነትንና ትጉህ መሆንን ሚጠይቅ እንደሆነ ቃሉ እራሱ ይጠቁመናል፡፡በእንደዚህ አይነት ጠበቅ ያለ ውሳኔና ጉጉት ውስጥ ስንሆን ብሎም በትእግስት ፊቱን ስንፈልግና እንደ ማርያም እግሩ ስር ስንቀመጥ በራሱ መንገድና አሰራር ተገልጾ በቃላት መግለጽ በሚያቅተንና በሚያስደንቅ ሁኔታ እራሱን ይገልጥልናል፡፡ይህን አባባል ስጽፍ በራሴ ህይወት የተከሰተውንና እራሱን የገለጠልኝን ሁኔታዎች እያስታወስኩ እንደሆነ ልብ እንድትሉልኝ እፈልጋለሁ፡፡ማለትም ዝም ብዬ ተረት እየጻፍኩ አይደለም፡፡በቅንነት ከፈለግነው በእርግጠኝነት እንደሚገኝ ማብሰሬ ነው፡፡


ስለዚህ ይህንን የነገስታት ንጉስ በማወቅ ፍጻሜያችን እንዲያምር ከተኛንበት እንነሳ እንከተለው፡፡ለምን ቢባል በርሱ ዘንድ እረፍት አለ፣ሞገስ አለ፣ ብዙ በረከትም አለ፡፡ ምሳ 8፡34-35 እንዲህ ይላል ፡-‹‹የሚሰማኝ ሰው ምስጉን ነው ዕለት ዕለት በቤቴ መግቢያ የሚተጋ፤የደጄንም መድረክ የሚጠብቅ፡፡እኔን ያገኘ ህይወትን ያገኛልና፤ከእግዚአብሔርም ሞገስን ያገኛልና፡፡››አዎ እርሱን መከተል ሕይወት ነው እረፍትም ነው፡፡ስለዚህ እርሱን ለማወቅ እንነሳ፣እንከተለው፣እንትጋ!እንዲህ ብናደርግ በእራሱ ጊዜ ተገልጦ ያስደንቀናል!!!